19/06/2026
በድህረ ምርጫ ወቅት የሲቪል ሰርቫንቱ ሚና ላይ ያተኮረ ውይይት በኢንስቲትዩቱ ተካሄደ።
፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨
ሰኔ 12 ቀን 2018 ዓ.ም የኢትዮጵያ ብቃትና ሥራ አመራር ኢንስቲትዩት አመራሮችና ሠራተኞች በድህረ ምርጫ ወቅት የሲቪል ሰርቫንቱ ሚና ላይ ያተኮረ የግማሽ ቀን ውይይት በኢንስቲትዩቱ ዋና መ/ቤትና በቢሾፍቱ ማሰልጠኛ ማዕከል አካሄዱ።
የመድረኩን ዓላማ አስመልክቶ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር አቶ ደሳለኝ ጣሰው በቅድሚያ ከምርጫ ጊዜው በፊት እና በምርጫው ሂደት ወቅት አስቻይ ሁኔታዎች እንዲፈጠር መደረጉ፤ ከ50 ሚሊዮን በላይ ዜጎችም ፍፁም ዲሞክራሲያዊ በሆነ መንገድ ያስተዳድረኛል ያሉትን መምረጥ መቻላቸው ኢትዮጵያ እንድታሸንፍ አድርገዋል ብለዋል።
እንደ ዋና ዳይሬክተሩ ገለፃ በ7ኛው ሀገራዊ ምርጫ የዲሞክራሲያዊ ሥርዓት በሀገራችን እየተገነባ መሆኑና ዜጎች ሁልጊዜ ለሀገሪቱ ሠላምና ፀጥታ ቅድሚያ የሚሰጡ መሆኑን የተማርንበትና ለሌሎች ሀገራት መልካም ገፅታችንን ያሳየንበት ነው ብለዋል።
የዛሬው መድረክም በቀጣዩ አዲስ ዓመት በመስከረም
ወር በምርጫ ቦርድ አሸናፊው ከተነገር በኋላ መንግስት የሚመስርተው ፓርቲ እስከሚታወቅና ርክክብ እስኪደረግ ድረስ በድህረ ምርጫ ወቅት እንደ ሲቪል ሰርቪስ ተቋም የሚጠበቁብን ተግባራት ላይ መወያያት እንደሆነ የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር በመክፈቻ ንግግራቸው አመላክተዋል።
የኢንስስቲትዩቱ የሰው ሀብትና ስትራቴጂክ ሥራ አመራር ጽ/ቤት ሥራ አስፈፃሚ አቶ አብዱልሃሊቅ ረሺድ በድህረ ምረጫ ወቅት ሲቪል ሰርቫንቱ ሊተገበሩ ስለሚገባቸው ዋና ዋና ተግባራትን በተመለከተ መነሻ ሐሳብ አቅርበው፤ የኢንስቲትዩቱ ሠራተኞችም መነሻ ሐሳቡን መሠረት በማድረግ ውይይት ከተካሄደ በኋላ የዕለቱ መድረክ ተጠናቋል።