08/08/2025
ብሔራዊ ባንክ በተባበሩት አረብ ኤምሬትስ የሚገኙ ህገወጥ የገንዘብ አስተላላፊዎችን አስጠነቀቀ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ መቀመጫቸውን በተባበሩት አረብ ኤምሬትስ (ዱባይ) ያደረጉ ድርጅቶች መደበኛውን ገበያ ያፈነገጠ የትይዩ ገበያውን የሚያስፋፉ ህገወጥ ድርጊቶች እንዳሉ ገልጿል። ባንኩም እነዚህን ድርጊቶች ለመግታት አስቸኳይ እርምጃ እንደሚወስድ አስታውቋል።
የብሔራዊ ባንክ ገዢ አቶ ማሞ ምህረቱ በወቅታዊ የውጭ ምንዛሪ ገበያ እንቅስቃሴን በተመለከተ በሰጡት መግለጫ ፤ የኢትዮጵያን የፋይናንስ ስርዓት ሆን ብለው ለመሸርሸር እና የገበያ ዋጋን ለማዛባት በማለም በውጭ ሀገር የሚገኙ የገንዘብ አስተላላፊ ድርጅቶች ላይ የሚወሰደው እርምጃ እንደሚቀጥል በጥብቅ አሳስበዋል።
ማዕከላዊ ባንኩ በህገወጥ መንገድ ኢ-መደበኛ ገበያን የሚጠቀሙ አካላት ከዚህ ድርጊታቸው ካልተቆጠቡ "ገንዘባቸውን እስከመውረስ" የሚደርስ እርምጃ እወስዳለሁ ማለቱን ካፒታል ከመግለጫው ተመልክቷል።
በተጨማሪም፣ የባንክ ስርዓቱን የማይጠቀሙ የንግዱ ማህበረሰብ አባላት በአፋጣኝ ወደ ባንክ ስርዓቱ እንዲገቡ በጥብቅ አሳስቧል።
ይህ እርምጃ ብሔራዊ ባንክ የሀገሪቱን የፋይናንስ ስርዓት ለማረጋጋት እና የውጭ ምንዛሪ አቅርቦትን ለመቆጣጠር የሚያደርገው ጥረት አካል መሆኑም ተመላክቷል።
Source: capitalethiopia