27/08/2026
በመኪና መሸጫዎቹ ጉዳይ የተወሰነው ውሳኔ ጥሩ እንደነበር መፃፌ ይታወሳል። መንግስት ህብረተሰቡ ላይ ዋጋ በሚያንሩና ተገቢውን ንግድ ፍቃድ ሳያወጡ በሚሰሩ የመኪና መሸጫ ቤቶች ላይ ገበያውን ለማረጋጋት የወሰደው እርምጃ የሚበረታታ ነው።
ሆኖም ይህ ውሳኔ ከተወሰነ በኋላ መሬት ላይ ያለውን ሁኔታ ለመታዘብ ችያለሁ። ከላይ እንዳልኩት ውሳኔው ጥሩ ሆኖ ይህ ሴክተር ግን ለብዙ ሺ ሰዎች የስራ እድል የፈጠረ ሴክተር እንደመሆኑ ቤቶቹ ሲዘጉ ብዙዎች ስራ ፈት ሆነዋል። ከነዚህ ውስጥ ቤተሰብ የሚያስተዳድሩ ሰዎች ይገኙበታል። ቤቶቹ ከመዘጋታቸው በፊት የተሰጠው ግዜ ጥቂት ከመሆኑ አንፃር ለብዙ ሰዎች ዱብዳ ነው የሆነው። መሸጫ ቤቶቹ ከሚቀጥሯቸው ሰዎች በዘለለ በየመኪና መሸጫ ቤቶቹ ስር የሚሰሩ ህጋዊ ደላሎች፣ ከመኪና አጣቢ ጀምሮ እስከ ፀሃፊ ሻጭና ጥበቃ አሁን ላይ ከስራ ውጪ ሆነዋልና ባለው የኑሮ ሁኔታ እሱ ታሳቢ ተደርጎ እነዚህ መሸጫ ቤቶች ወደህጋዊ መስመር የሚገቡበት ሁኔታ ቢመቻች ጥሩ ነው ብዬ አስባለሁ።
በህገወጥ አሰራሮች ላይ ፈጣንና ቆራጥ እርምጃ መውሰድ እንዳለ ሆኖ ያንን ተከትሎ የሚፈጠሩ ማህበራዊ ቀውሶችም ታሳቢ ተደርገው በዘርፉ ላይ ላሉ ሰዎች ስህተቶቻቸውን አርመው ወደስራ የሚመለሱበት መንገድ ቢመቻችላቸው ባይ ነኝ።
Natnael Mekonnen Yitna