06/11/2022
ዝክረ ክቡር ዶ/ር አርቲስት ዓሊ መሐመድ ሙሣ ( ዓሊ ቢራ)
ከ50 ዓመታት በላይ በሙዚቃ ዓለም በመቆየት ዘመን ተሻጋሪ የሙዚቃ ስራዎቹን ለሕዝብ በማድረስ ከፍተኛ ዝናና ተቀባይነት ያተረፈውን ድምፃዊ ዓሊ ቢራ (የክብር ዶ/ር) በዛሬው ዕለት ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል።
ዓሊ ቢራ የተወለደው መስከረም 15 ቀን 1940 ዓ/ም በድሬዳዋ ከተማ ነው። በህጻንነቱ የተለያዩ የአገር ውስጥ እና ዓለም አቀፍ ሙዚቃዎችን እያደመጠ ያደገው ዓሊ ለትምህርት ቤት ጓደኞቹና ለቤተሰቦቹ በማንጎራጎር ነበር የሙዚቃ ህይወቱን የጀመረው። በድሬደዋ ውስጥ ብዙ ቋንቋዎች መኖር ያልገደበው ዓሊ በዐረብኛ፣ ኦሮምኛ፣ አደርኛና ሶማሊኛ ሙዚቃዎችን ይጫወት ነበር።
ከዚያም በ14 ዓመቱ አፍራን ቃሎ የተባለ የኦሮሞን ሙዚቃ ለማስተዋወቅ አላማ ያደረገ የባህላዊ ሙዚቃ ቡድንን ተቀላቀለ።
የገንደቆሬው ዓሊን ወላጆቹ ያወጡለት ስም ዓሊ መሐመድ ሙሳ ብለው ነው።
በኋላ ዓሊ ቢራ ተባለ። ይኸውም በአፍራን ቃሎ ቡድን ውስጥ ሌላ ዓሊ የተባለ ልጅ በመኖሩ ሁለቱን ለመለየት ዓሊ መጀመሪያ ካዜመው "BIRRAA DHAA BARIHE" "ቢራ ዳ ባሬ" የሚለው ዘፈኑ "ቢራ" የሚለው ተወስዶ "ዓሊ ቢራ" ተባለ። ወደ አዲስ አበባ በመሄድ የተለያዩ ባንዶች ውስጥ የተጫወተው ዓሊ በ1976 ዓ/ም ከስዊድናዊት ዲፕሎማት ባለቤቱ ጋር ከኢትዮጵያ በመውጣት ኑሮውን በውጭ ሃገር አደረገ።
ዓሊ ቢራ የመጀመሪያ ትምህርቱን በመድረሳ ጅዳ እና በልዑል መኮንን ትምህርት ቤት፤ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ደግሞ ወደ አዲስ አበባ በመሄድ በካቴድራል ትምህርት ቤት ተከታትሏል። አሜሪካ በሚገኘው የሳንታ ሞኒካ ኮሌጅም የሙዚቃ ትምህርትም ተከታትሏል።
ዓሊ ቢራ በ1955 ዓ/ም ድሬዳዋ ውስጥ በአፍረን ቃሎ ባንድ አጃቢ ዘፋኝ በመሆን ከሰራ በኋላ በክቡር ዘበኛ ኦርኬስትራ ተቀጥሮ ለ3 ዓመታት በድምፃዊነት ተጫውቷል። ችሎታው እየጎለበተ ሲሄድም አይቤክስ ባንድን በመቀላቀል ለ8 ዓመታት የሙዚቃ ሥራዎቹን በዲአፍሪክ ሆቴል ሲያቀርብ ቆይቷል።
ዓሊ ቢራ በአጠቃላይ 264 የሚደርሱ ዘፈኖችን የተጫወተ ሲሆን፤ ለህትመት ያበቃቸው የካሤት አልበም ቁጥር ግን 6 ብቻ ነው።
ዓሊ ቢራ በዘፈኖቹ ፖለቲካዊ ጉዳዮች እያነሳ በመጫዎትም ይታወቃል። ስለዚህም ሲናገር
"በቋንቋችን ላይ የነበረው ጫና ትንሽ የበዛ ነበር። እኔ ኢትዮጵያዊ ነኝ። ግን ደግሞ ኦሮሞም ነኝ። የነበረው ስርዐት ግን ይሄን አይቀበለውም። ከሌሎች በተለየ ኦሮሞ እና ኦሮምኛ ቋንቋ ላይ የተለየ ተፅዕኖ ነበረው። ስለዚህ በወቅቱ የነበረውን ነገር በመንቀፍ እዘፍን ነበር" ብሏል።
ዓሊ ቢራ ከመዝፈንም ባሻገር ፒያኖ፣ ጊታርና ኡድ የመሳሰሉትን የሙዚቃ መሣሪያዎችንም ይጫወታል፣ 8 ያህል ቋንቋዎችንም ይናገራል። ኦሮምኛ፣ አማርኛ፣ ሶማልኛ፣ አፋርኛ፣ ሃረሪኛ፣ ዐረብኛ እና እንግሊዝኛ በዋናነት ይጠቀሳሉ።
ዓሊ ቢራ የኃምሣ ዓመት የሙዚቃ ህይወቱ የወርቅ ኢዮቤልዮ " መማር አሁንም መማር " በሚል በደመቀ ሁኔታ ተከብሮለታል።
ዓሊ ጤንነቱን በተመለከተ በጭንቅላቱ ላይ በበቀለ ዕጢ ምክንያት የግራ ዐይኑ ማየት እንዳቆመ እና የቀኙም እንደተዳከመበት፣ እግሩም በካንሠር ተጠቅቶ የነበረ ቢሆንም በቀዶ ጥገና ህክምና ድኖለት ነበር።
ዓሊ ቢራ ለራሱ እና ለሌሎች ድምፃውያን በርካታ ግጥም እና ዜማዎችን ደርሷል፡፡ የራሱን ለየት ያለ የአዘፋፈን ስልትም ፈጥሯል፡፡ በሀገራችን ታሪክ ታላላቅ ከሚባሉ የሙዚቃ ቡድኖች ጋርም ሰርቷል፡፡ በሀገር ውስጥ እና በውጪም በዛ ባሉ መድረኮች ላይ ተጫውቷል፡፡ በሙዚቃው ዓለም በቆየባቸው ዘመናት በሀገር ውስጥ እና በዓለም አቀፍ ደረጃ የህዝብ ፍቅር እና አክብሮትን ተቀዳጅቷል፡፡ በርከት ያሉ ሽልማቶችንም አግኝቷል፡፡ ከጅማ ዩኒቨርስቲ የተሰጠው የክብር ዶክትሬትም ከእነዚህ ውስጥ አንዱ ነው፡፡
ክቡር ዶክተር ዓሊ ቢራ ከሙዚቃው ጎን ለጎን “Birra Children’s Education Fund” የተባለ ምግባረ ሰናይ ድርጅት ከባለቤቱ ጋር አቋቁሞ ለህፃንት ትምህርት ድጋፍ ያደረግ ነበር፡፡ ድርጅቱ በድሬዳዋ አካባቢ ባሉ ት/ቤቶች ላይ እየሰራ ሲሆን በመላው የሀገሪቱ ክፍሎች የተጠናከረ ስራ ለመስራት እቅድ ነበረው፡፡
የ73 ዓመት ዕድሜ ባለፀጋውን ዓሊ ቀደም ብሎ የጂማ ዩኒቨርሲቲ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ያበረከተለት ሲሆን የትውልድ ከተማው የድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ ደግሞ ቅዳሜ ሰኔ 29 ቀን 2011 ዓ/ም ተጨማሪ የክብር ዶክትሬት ዲግሬ አበርክቶለት ነበር።
የአንጋፋው የሙዚቃ ሰው የክቡር ዶ/ር ዓሊን ነፍስ ይማር
ለቤተሰቦቹ፣ ለወዳጅ እና አድናቂዎቹ መፅናናት ይሁን ‼