14/10/2024
ስለ ሰንደቅ ዓለማ ቀን እውነታዎች
*************
ሰንደቅ ዓላማ ምንድን ነው?
ሰንደቅ ዓለማ የሉዓላዊ ሀገር መለያ አርማ እና የህዝቦች ማንነት መገለጫ ነው፡፡ የህዝቦች ታሪክና አንድነት መገለጫ እና የሀገር ምልክትም ነው፡፡ ሰንደቅ ዓለማ የሰላም፣ የድል አድራጊነት እና የስኬት መገለጫ ተደርጎ ከፍ ብሎ ይውለበለባል፡፡ ሀገራት ካላቸው ሀገራዊ ታሪክና ዳራ ጋር አያይዘው ለሰንደቅ ዓለማቸው ያላቸውን ፍቅር እና ክብር በማሳየት ያከብሩታል፡፡
እንደ ኢትዮጵያ ያሉት ጥንታዊ እና ነጻ ሀገራት የድል ቀናቸውን፣ በቅኝ ግዛት የተያዙት ሀገራት ደግሞ ከቅኝ ግዛትነት ነጻ የወጡበትን ቀን፣ በተለያዩ ምክንያት ዘግይተው ሀገር የሆኑት ደግሞ ነጻና ሉዓላዊ መንግሥት የመሰረቱበት ቀን ለማስታወስ የሰንደቅ ዓለማ ቀን ያከብሩታል፡፡
በዓለማችን 52 ሀገራት የሰንደቅ ዓለማ ቀንን ያከብራሉ፡፡ ኢትዮጵያም በራሷ መንገድ የሰንደቅ ዓለማን ቀንን ሀገራዊ መልክና ይዘት ያላቸው መልእክቶችን ቀርጻ በደማቅ ሁነቶች ታከብራለች፡፡ በዓሉ ጥቅምት በገባ በመጀመሪው ሳምንት ሰኞ ይከበራል፡፡ ኢትዮጵያ ላለፉት 16 ዓመታትም የሰንደቅ ዓለማ ቀንን በተለያዩ መሪ ቃሎች ስታከብር ቆይታለች፡፡ በዓሉ በየዓመቱ በደማቅ ሁኔታ በፌዴራል ደረጃ፣ በክልሎች፣ በከተማ አስተዳደሮች እና በሁሉም የፌዴራልና ክልል ተቋማት ሁሉን አቀፍ በሆነ መልኩ ይከበራል፡፡
ኢትዮጵያ ባለፉት 16 ዓመታት ቀኑን በሀገር አቀፍ ደረጃ ስታከብር ምን ዓይነት መልእክቶችን ተጠቅማ ነበር? ባለፉት 16 ዓመታት የሰንቅ ዓላማ ቀናት አከባበሮች በሰንደቅ ዓለማው መርሆች እና ለብዘኃነታቸው ባላቸው ትርጉም ዙሪያ ግልጽነት ለመፍጠር፣ ዜጎች በሰንደቅ ዓለማው ትርጎሜ እና ቅርጽ ተመሳሳይ ግንዛቤ እንዲያዳብሩ ለማድረግ፣ የተዛቡ እና አሉታዊ አስተሳሰቦችን ለማቃናት ለማረም የሚያስችሉ መልዕክቶች ተላልፈውባቸዋል፡፡
የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓለማ አረንጎዴ፣ ቢጫ፣ ቀይ ቀለማት ያሉት ሲሆን መሃሉ ላይ ሰማያዊ ኮከብ መደብ ብሔራዊ አርማ ያለው ሰንደቅ ዓለማችን ልምላሜያችንን፣ ተስፋችን እና ለሀገር ሉዓላዊነት የሚከፈል መስዋእትነት ያንጸባርቃል፡፡
በኢትዮጵያ እስከ አሁን የተከበሩ የሰንደቅ ዓለማ ቀኖችን አስመልክቶ የተንጸባረቁ መሪ ሀሳቦችን በከፊል እናስታውስ፡-
• 7ተኛው "በህዝቦቹዋ ተሳትፎና ትጋት ድህነትን ድል በመንሳት ብሄራዊ ክብራችንና ሰንደቅዓለማችንን ከፍ ከፍ በማድረግ ላይ ያለች ሀገር ኢትዮጵያ!"
• 10ኛው "ራዕይ ሰንቀናል ለላቀ ድል ተነስተናል!"
• 11ኛው "ሰንደቅ ዓላማችን ለዴሞክራሲያዊ አንድነታችን!”
• 12ኛው "ሰንደቅ ዓለማችን የብዙሃን ድምር ውጤት፣ የአንድነታችን ምሶሶ ነው!”
• 13ተኛ "ሰንደቅ ዓለማችን ፣ለሰላማችን፣ ለአንድነታችን፣ ለሀገራዊ ብልጽግናችን!"
• 14ኛ "በአዲስ ምዕራፍ በተሟላ ሉዓላዊነት ለሰንደቅ ዓለማ ከፍታ!"
• 15ኛ "ሰንደቅ ዓላማችን የብዘሃነታችንና የሉዓላዊነታችን ምሶሶ ነው!”
• 16ኛ "የሰንደቅ ዓለማችን ከፍታ ለህብረ ብሄራዊ አንድነታችንና ሉዓላዊነታችን ዋስትና ነው!"
• 17ኛ "ሰንደቅ ዓላማችን ለብሔራዊ አንድነታችን፣ ለሉዓላዊነታችንና ለኢትዮጵያ ከፍታ!”