ወሎ የአካባቢ ተጽዕኖ ግምገማ -Wollo EIA

ወሎ የአካባቢ ተጽዕኖ ግምገማ -Wollo EIA Contact information, map and directions, contact form, opening hours, services, ratings, photos, videos and announcements from ወሎ የአካባቢ ተጽዕኖ ግምገማ -Wollo EIA, Business consultant, Dessie.

18/03/2022

Amhara National Regional State Environment and Forest Protection Authority
4 ኤፕሪል 2019 ·
የአካባቢ ተፅዕኖ ግምገማ መመሪያ ቁጥር 001/2010 ክፍል 2 የቀጠለ……………..
1 የአካባቢ ተጽዕኖ ግምገማ ሪፖርት ዝግጅት
የሚዘጋጀው የአካባቢ ተፅእኖ ግምገማ ሪፖርት የኘሮጀክቱን አሉታዊና አወንታዊ ተጽዕኖዎች የለየ፣ ፕሮጀክቱ ሲተገበር ስለሚወሰዱ የአካባቢ ተጽዕኖ ማቃለያ እርምጃዎች በቂ መረጃ የያዘ መሆን አለበት፡፡ የፕሮጄክቱ ባህሪ የሚያስገድድ ካልሆነ በቀር ሪፖርት የሚቀርበው በአማርኛ ቋንቋ ይሆናል፡፡
የፕሮጄክቱ ባለቤት የውጭ አገር ዜግነት ያለው ከሆነ በእንግሊዝኛ ሪፖርት ሊቀርብ ይችላል፡፡ ሆኖም ግን ከሚቀርበው ሪፖርት ውስጥ የአካባቢ አያያዝና የክትትል እቅዱ ክፍል በአማርኛ ተተርጉሞ የሪፖርቱ አካል ሆኖ ይቀርባል፡፡ የአካባቢ ተጽዕኖ ጥናት ዘገባ ሲዘጋጅ መካተት የሚገባቸዉ ዝርዝር ጉዳዮች የሚከተሉት ይሆናሉ፡-
1.1 አጠቃላይ መግለጫ (Executive Summary)
ይህ ክፍል ከሁለት ገጽ ያልበለጠ ሆኖ የፕሮጀክቱ ገምጋሚዎችና ውሳኔ ሰጭ አካላት የፕሮጀክቱን ምንነት፣ ተጽዕኖዎችንና የተጽእኖ ማቃለያ መንገዶችን በቀላሉ እንዲረዱት የሚያስችል ክፍል ነው፡፡ በመሆኑም አጠቃላይ መግለጫው ስለፕሮጀክቱ ግልፅ፣ ትክክለኛና የማይጣረስ መረጃ ሊይዝ ይገባል፡፡
ይህ ክፍል ገምጋሚዉ የውሳኔ ሀሳብ ለመስጠት የሚያግዙትን ዋና ዋና ግኝቶችና ምክረ-ሀሳቦች የሚዳስስበት ክፍል ነው፡፡ በዚህ ክፍል የሚከተሉት ጉዳዮች መካተት ይኖርባቸዋል፡- የፕሮጀክቱ ስምና አድራሻ (መገኛ ቦታ)፤ የፕሮጀክቱ ባለቤት ስም፤ ጥናቱን ያጠናው አማካሪ ድርጅቱ ስም፤ የፕሮጀክቱ ምንነት አጭርና ግልጽ ማብራሪያ፤ የፕሮጀክቱ ቦታ አጭርና ግልጽ የመነሻ መረጃ፤ የፕሮጀክቱ አማራጮች፤ በፕሮጀክቱ ምክንያት ይከሰታሉ ተብሎ የሚገመቱ ዋና ዋና የአካባቢ ተፅእኖዎች፤ የተለዩ የተጽእኖ ማቅለያ ዘዴዎች (የገንዘብ ወይም በአይነት ካሳን ጨምሮ)፣ የአካባቢ ክትትል ስራዎችና የማስተግበሪያ ስልት፡፡
1.2 መግቢያ (Introduction)
ይህ ክፍል የፕሮጀክቱ አጠቃላይ የመነሻ ሀሳብ የሚገለጽበትና የአካባቢ ተፅዕኖ ጥናቱ አደረጃጀት የሚመላከትበት ክፍል ሲሆን ጽሁፉ ከሁለት ገጽ መብለጥ የለበትም፡፡ የጥናቱም መግቢያ የሚከተሉትን ነጥቦች በግልፅ ማሳየት ይኖርበታል፡፡
1) የፕሮጀክቱ ወይንም የጥናቱ መነሻ ሀሳቦች፤
2) የፕሮጀክቱ ፕሮፖዛል መግለጫ ባጭሩ (ዓላማ፣ የፕሮጀክቱ መገኛ ቦታ፣ የተለዩ አማራጮች ለምሳሌ ከቦታ፣ ከዲዛይን፣ ከአሰራር ሂደት፣ ከሚጠቀምበት ቴክኖሎጂ፣ ከግብዓትና ጥሬ ዕቃ አንጻር ወዘተ፣ የሚጠይቀውን የኃይል ዓይነት፣ ፍጆታና ምንጭ እንዲሁም የሌሎች ሃብቶችን ፍላጎትና የፕሮጀክቱን የቆይታ ጊዜ)፤
3) የአካባቢ ተጽእኖ ጥናት ዘገባው አደረጃጀት፤
4) የጥናት ዘገባው አላማ፣ የባለሀብቱን ግዴታ፣ የህግ ተጠያቂነትንና በቀጣይ የሚከናዎኑ ተግባራትን የሚያገልጽ መሆን አለበት፡፡
1.3 የአካባቢ ተጽእኖ ጥናቱ ዓላማ
ከፕሮጀክቱ ትግበራ በፊት የአካባቢ ተጽዕኖ ጥናት ማካሄድ ያስፈለገበት ጥቅል አላማና የአካባቢ ተጽዕኖ ጥናቱ የሚያረጋግጣቸው ዝርዝር አላማዎች በዚህ ክፍል በአግባቡ ሊገለጹ ይገባቸዋል፡፡ የአካባቢ ተጽዕኖ ጥናቱ በዚህ ክፍል ለተለዩት ዝርዝር አላማዎች ምላሽ የሚሰጥ መሆን አለበት፡፡
1.4 የጥናቱ ወሰን
ፕሮጀክቱ የአካባቢ ተጽእኖ ጥናት የሚያስፈልገዉ ከሆነና የአካባቢ ወሰን ልየታ ጥናት የተካሄደለት ከሆነ በዚህ ጥናት በተካተተዉ ቢጋር ውስጥ የጥናቱ ጥልቀትና ስፋት በግልጽ መጠቀስ ይኖርበታል፡፡ ፕሮጀክቱ የአካባቢ ተጽእኖ ጥናት ማካሄድ የሚያስፈልገው ከሆነ የጥናቱ ወሰን እንደ ፕሮጀክቱ አይነትና ፕሮጀክቱ እንደሚተገበርበት አካባቢያዊ፣ ማህበራዊ፣ ባህላዊና ኢኮኖሚያዊ ሁኔታ ተለይቶ መቀመጥ ይኖርበታል፡፡ የጥናት ወሰኑ የፕሮጀክቱን የጥናት ክልል የሚያሳይ ካርታ ሊያካትት ይገባዋል፡፡
1.5 የጥናቱ ስልት ወይም ዘዴ
በዚህ ክፍል አወንታዊና አሉታዊ የአካባቢ ተፅእኖዎችን ለመለየት፣ ለመተንበይና ለመተንተን፣ እንዲሁም ያሉ አማራጮችንና የማቃለያ እርምጃዎችን ለመለየትና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን ለማሳተፍ ጥቅም ላይ የሚውሉ ዘዴዎች የሚገለጽበት የዘገባ ክፍል ነው፡፡ በመሆኑም በዚህ ክፍል የሚከተሉትን ነጥቦች በግልፅ ማስቀመጥ ይገባል፡-
1) ጥናቱን ለማካሄድ ጥቅም ላይ የሚውል የጥናት ስልት፣
የሚያስፈልግ ግብዓት፣ የመረጃ መሰብሰቢያ ዘዴዎችና የትንተና ዘዴዎች (ለምሳሌ የባለሙያዎች ሙያዊ አስተያየት፣ የአዋጭነት ትንተና፣ የመገምገሚያ ቅፆች፣ ከአሁን በፊት ያሉ ልምዶች፣ የቦታ ሽፋን፣ ወዘተ)
2) የሚመለከታቸውን አካላት ለማሳተፍ ጥቅም ላይ የሚውል የማሳተፊያ ዘዴ ወይም ስልትና የተሳትፏቸው ደረጃ
3) በጥናቱ የሚሳተፉ ባለሙያዎች ብዛት፣ የሙያ ስብጥር፣ ኃላፊነትና ሙሉ አድራሻ
1.6 በጥናቱ ወቅት የተወሰዱ ታሳቢዎች እና የነበሩ የእውቀት ክፍተቶች
በቂ የመረጃ ምንጭ ባለመገኘቱ የተነሳ ሊተገበር በታሰበው ፕሮጀክት ዙሪያ የሚሰበሰቡ መረጃዎች ከአጠራጣሪ ምንጮች ሊሰበሰቡ ይችላሉ፡፡ በዚህ ምክንያት አንዳንድ የጥናት ዳሰሳዎች በግምት ወይም በመላምት ላይ ተመርኩዘው ሊሰሩ ስለሚችሉ ተፅእኖዎችን ለመተንበይና ለመተንተን ክፍተት ሊገጥም ይችላል፡፡ ስለዚህ ጥናቱን የሚያዘጋጀው አካል የሚከተሉትን ነጥቦች በማካተት የዳሰሳ ጥናቱን የእርግጠኛነት ደረጃ በግልፅ ማመላከት ይኖርበታል፡፡ በዚህ ክፍል፡-
1) በጥናት ሂደት ያጋጠሙ የእውቀት ክፍተቶችን፣ በይሆናል የተወሰዱ መረጃዎችንና የመረጃ ምንጭ ያልተገኘላቸውን ጉዳዮች ይለያሉ፣
2) መላምቶች ያልተሟሉ የሆኑበትን ምክንያት ይዘረዘራል
3) የተለዩት የእውቀት ክፍተቶችና መላምቶች በውሳኔ አሰጣጥ ላይ የሚኖራቸው እንድምታ
4) ያጋጠሙ እጥረቶችንና ውስንነቶችን ለማስወገድ የተወሰዱ መፍትሄዎች መገለጽ ይኖርባቸዋል፡፡
1.7 የፖሊሲ፣ የህግና የአስተዳደር ማዕቀፎች
ይህ ክፍል ፕሮጀክቱ ሲተገበር ሊፈጽማቸውና ሊመራባቸው የሚገቡ የፖሊሲና ህጋዊ ማዕቀፎችን የሚዘረዝር የአካባቢ ተጽዕኖ ግምገማ ሪፖርት ክፍል ሲሆን ፕሮጄክቱን ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችሉ የፖሊሲ፣ የህግና የአካባቢ ደረጃ ማዕቀፎች በጥናቱ ይዳሰሳሉ፡፡ ከቦታውና ከፕሮጀክቱ ጋር ተገቢነትና ተያያዥነት ያላቸው ተጨማሪ የህግ ክፍሎች በዕዝል ይያያዛሉ፡፡
1.8 የፕሮጀክቱ ገለፃ
በዚህ ክፍል የሚከተሉት ነጥቦች መካተትና መገለፅ አለባቸው፡-
1) የፕሮጀክቱ ስፋትና ባህሪ፣
2) ለፕሮጀክቱ የተለያዩ አማራጮች ግልፅ ማብራሪያ፣
3) የጥሬ እቃዎች ምንጭ፣ አይነት፣ ባህሪና መጠን፣
4) በምዕራፎች የተከፋፈለ የፕሮጀክቱ የትግበራ የጊዜ ሰሌዳ፣
5) የቴክኖሎጂ አይነትና የቴክኖሎጅ አጠቃቀም ገለጻ፣
6) የአመራረት ሂደት፣ የተረፈ-ምርቶችና ዋና ምርቶች አይነትና መጠን
7) የደረቅና ፍሳሽ ቆሻሻ የማፅዳትና የማስወገድ ስርዓት፣
😎 የሰውና የግብዓት ፍጆታ ወጪዎች፣
1.9 የባዮፊዚካልና ማህበረ-ኢኮኖሚ መሰረታዊ መረጃዎች ትንተና
በዚህ ክፍል የፕሮጀክቱን አካባቢዊ ሁኔታ የሚገልፅ መሰረታዊ መረጃ በመሰብሰብ አካባቢውን በትክክል የሚያሳይ ዘገባ ማዘጋጀት ያስፈልጋል፡፡ ይህ ክፍል በፕሮጀክቱ ምክንያት ጉዳት ወይም ተጽዕኖ ስለሚደርስባቸው አካባቢዎች ትኩረት በመስጠት ግልፅ ማብራሪያ ማካተት/መስጠት ይጠበቅበታል፡፡ በመሆኑም መካተት የሚገባቸው መረጃዎች፡-
1) ፕሮጀክቱ የሚተገበርበትን ልዩ ቦታ የሚመለከት መረጃ (ለምሳሌ የአካባቢውን የመሬት ስሪት ወይም የይዞታ ሁኔታ፣ በዙሪያው ስለሚገኝ የመሬት ሁኔታ፣ በአካባቢው ላይ ያሉና በግልፅ የሚታዩ ተግዳሮቶች፣ በፕሮጀክቱ ውስጥና በአካባቢዉ ያለው የመሰረተ-ልማት አገልግሎት ሁኔታ ወዘተ)፣
2) አሃዛዊና አሃዛዊ ያልሆኑ ፊዚካላዊና ስነ-ህይወታዊ የአካባቢ መረጃዎች (ለምሳሌ፡- የአየር ንብረት፣ የአፈር፣ የውሃ ሀብት፣ የስርዓተ ምህዳር፣ የመሬት አቀማመጥ፣ የዕፅዋትና የእንስሳት አይነት ስርጭትና ብዛት ወዘተ…….)፣
3) አሃዛዊና አሃዛዊ ያልሆኑ የማህበራዊና ምጣኔ ሃብታዊ መረጃዎች (ለምሳሌ የህዝብ ቁጥርና ስርጭት፣ የዕድሜ ስብጥር፣ የኢኮኖሚ እድገት ሁኔታ፣ የውልደትና የጤና ሁኔታ፣ የቤተሰብ የገቢ ሁኔታ መረጃ፣ የኑሮ ሁኔታ፣ የመሰረተ-ልማት አገልግሎት፣ የቤቶች ሁኔታ፣ የሃይል ፍጆታ፣ የውሃ አቅርቦት ወዘተ…..)
4) የባህላዊና ታሪካዊ ቦታዎች ገለጻ (ለምሳሌ ብሄራዊ ፓርኮች፣ የዱር እንስሳት መጠለያ ቦታዎች፣ የመስህብ ቦታዎችና ሃውልቶች፣ በሰውና በእንስሳት ምስል የተሰሩ ሀውልቶች፣ ትኩረት የሚሰጣቸው ሃይማኖታዊ ቦታዎች ወዘተ…..)፣
5) ተጽዕኖ የሚደርስበትን ቦታ የሚያመለክቱ ኮኦርድኔቶች፣ ከለር ፎቶግራፎች፣ ሰንጠረዥና ሌሎች ገላጭ መረጃዎች፣
6) የፕሮጀክቱ የትግበራ ቦታ ካርታና የፕሮጀክት ሳይት ፕላን፣
7) ፕሮጀክቱ ድንበር ተሻጋሪ ተፅዕኖ የሚያደርስ ከሆነ ተጽእኖ የሚደርስበት አካባቢ የፊዚካላዊና ስነ-ህይወታዊ እንዲሁም የማህበራዊና ምጣኔ ሃብታዊ መረጃዎች ናቸው፡፡
1.10 የአካባቢ ተጽዕኖ ትንተና ማካሄድ
ይህ ክፍል አዎንታዊና አሉታዊ የአካባቢ ተፅእኖዎች የሚለይበት፣ የሚተነበይበትና የሚተነተንበት ወሳኝ ክፍል ነው፡፡ የእያንዳንዱ ተፅእኖ ትንተና የሚከተሉትን ነጥቦች ሊያካትት ይገባል፡-
1) የእያንዳንዱ ተጽእኖ ግልጽ ማብራሪያና ትንታኔ (ምሳሌ የተፅዕኖው መጠን፣ የቦታ ስፋት፣ የሚቆይበት ጊዜ፣ ድግግሞሽ፣ ደረጃ፣ ተጽእኖ የደረሰበት አካባቢ ወደነበረበት መመለስ የሚቻል መሆኑና አለመሆኑ፣ ስጋትና ያልተጠበቁ ሁኔታዎች ክስተት፣ ተጽዕኖ የሚደርስባቸው ክፍሎች መጠን ወዘተ) መለየት፣
2) በፕሮጀክቱ ውስጥና አካባቢ የሚገኙ ተጽዕኖ የሚደርስባቸው አካላት ትንተና፣
3) ፕርጀክቱን ለመተግበር የተለዩ አማራጮች ንጽጽር (ስፋት/መጠን፣ መገኛ ቦታ፣ ቴክኖሎጂ፣ ፕላን፣ የሃይል ምንጭ፣ የጥሬ እቃዎች ምንጭ፣ ቴክኒካዊ ተፈጻሚነት፣ የአካባቢዊና ማህበራዊ ችግሮች/እጥረቶች)፣
4) አዲሱ ፕሮጀክት ከነባር ፕሮጀክቶችና ወደፊት ሊሰሩ ከታቀዱ ፕሮጀክቶች ጋር ሲዳመር ሊደርስ የሚችለውን ተዳማሪ የአካባቢና ማህበራዊ ተጽዕኖ፣
5) የተጽዕኖ ትንበያ የእርግጠኛነት ደረጃ፣
6) የተሻሉ አማራጮችን ለመምረጥ የተሰበሰቡ መረጃዎች ምዘና ናቸው፡፡
1.11 የተፅዕኖ ማቅለያ እርምጃዎች
በፕሮጀክት ትግበራ ወቅት ጉዳት የሚያስከትሉ የፕሮጀክቱን ተግባራት ሙሉ በሙሉ ማስወገድ ቀዳሚ አማራጭ ተደርጎ መወሰድ ሲኖርበት ይህን ማድረግ ካልተቻለ ግን የተፅእኖ ማቃለያ ተግባራት በሚከተለው መልኩ ተዘርዝረው መቀመጥ ይኖርባቸዋል፡፡
1) ለእያንዳንዱ ተፅእኖ በእያንዳንዱ የፕሮጀክት የትግበራ ደረጃ ሊተገበሩ የሚገባቸው የተጽዕኖ ማቅለያ እርምጃዎች በአግባቡ ሊዘረዘሩና የሚያስፈልጋቸውም ወጪ (ገንዘብ) በበቂ ሁኔታ ሊመደብ ይገባል፡፡
2) የተለያዩ የማቃለያ እርምጃዎችን በመለየትና በማደራጀት ከተዘረዘሩት አማራጮች ውስጥ ምክንያታዊ በመሆን የተሻሉ የማቅለያ እርምጃዎችን በመምረጥ ማሳየት ያስፈልጋል፡፡
3) አዎንታዊ ተፅእኖዎችንም እንዴት የበለጠ ማሳደግ ወይም ማሻሻል እንደሚቻል በዚህ ክፍል መገለጽ አለበት፡፡
1.12 የአካባቢ አያያዝ እቅድ
1) ይህ እቅድ ከተጽዕኖ ማቃለያ እርምጃዎች የሚቀዳ ሲሆን የሚከናወኑ ተግባራትን በአግባቡ የለየ፣ ፈጻሚ ባለቤት ያለው፣ ሊተገበር የሚችል፣ አፈጻጸሙ የሚለካ፣ ግልጽ የሆነ የአሰራር ስርዓት ያለው፣ በቂ በጀት ያለውና በጊዜ የተገደበ ሆኖ በተለያዩ የፕሮጀክት የትግበራ ምዕራፎች ወቅት አካባቢውን ለመጠበቅ የሚያስችል ዝርዝር አቅድ የሚዘጋጅበት የአካባቢ ተጽዕኖ ግምገማ ሪፖርት ክፍል ነው፡፡
2) በእቅዱ ውስጥ የሚካተቱ ዋና ዋና ነጥቦች የሚከተሉት ሊሆኑ ይገባል፤
1) የተጽእኖዎች ዝርዝር
2) ለእያንዳንዱ ተጽእኖ የታቀዱ የተጽእኖ ማቅለያ ተግባራት ዝርዝር
3) የታቀዱ የተጽእኖ ማቅለያ ተግባራት መለኪያ
4) የታቀዱ የተጽእኖ ማቅለያ ተግባራት መጠን
5) ለእያንዳንዱ ተጽእኖ ማቅለያ ተግባራት የተመደበ ገንዘብ መጠን
6) የታቀዱ የተጽእኖ ማቅለያ ተግባራት የሚተገበሩበት የጊዜ ሰሌዳ
7) የታቀዱ የተጽእኖ ማቅለያ ተግባራትን የሚፈፅሙ አካላት ዝርዝር
) አንድ የአካባቢ አያያዝ እቅድ የቆያታ ጊዜ ጣሪያ 10 ዓመት ሆኖ በጸደቀ በአንድ አመት ጊዜ ውስጥ መተግበር መጀመር አለበት፡፡ በዚህ የጊዜ ገደብ ውስጥ ተግባራዊ እንቅስቃሴ ካለተጀመረ ጥናቱ ውድቅ ሆኖ እንደገና እንዲጠና ይደረጋል፡፡ አንድ የአካባቢ ተጽዕኖ ግምገማ ሪፖርት ሲዘጋጅ የፕሮጀክቱን ቅድመ ግንባታ፤ ግንባታ፤ ትግበራና መዝጊያ ወቅት ታሳቢ ያደረገ መሆን ይገባዋል፡፡ ከአስር አመት የጊዜ ቆይታ በኋላ የአካባቢ ጥናት ዘገባው መከለስ ወይንም ደግሞ በአዲስ መዘጋጀት ይኖርበታል፡፡
4) የአካባቢ አያያዝ እቅድ ፎርማት በእዝል 15.1 የተያያዘ ሲሆን የሚዘጋጀው የአያያዝ እቅድ ከላይ የተጠቀሱትን ዝርዝር መረጃዎች መያዝ ይኖርበታል፡
5) የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮና ሌሎች የሚመለከታቸው የስራና የግንባታ ፈቃድ ሰጭ አካላት በምድብ አንድና ሁለት ለተካተቱ የልማት ፕሮጀክቶች (በአብክመ የተሻሻለውን የአካባቢ ተፅዕኖ ግምገማ የአሰራር መመሪያ ዕዝል አንድን ይመልክቱ) የአካባቢ ተጽእኖ ግምገማ ሪፖርት ካልተዘጋጀላቸውና የአካባቢ ይሁንታ ፈቃድ ካልተሰጣቸው በስተቀር የግንባታ/ የስራ ፈቃድ መስጠት የለባቸውም፡፡
6) የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮና ሌሎች የሚመለከታቸው ፈቃድ ሰጭ አካላት በምድብ አንድና ሁለት ለተካተቱና የአካባቢ ይሁንታ ፈቃድ ለተሰጣቸው ፕሮጀክቶች የግንባታ/የስራ ፈቃድ በሚሰጡበት ጊዜ በተጽዕኖ ጥናት ዘገባው ውስጥ የተካተቱ የተጽዕኖ ማቃለያ ተግባራት በቀረበው ዲዛይን/የትግበራ ሂደት ውስጥ መካተቱን የማረጋገጥ ግዴታ አለባቸው፡፡
ይቀጥላል............

18/03/2022

Amhara National Regional State Environment and Forest Protection Authority
4 ኤፕሪል 2019 ·
የአካባቢ ተፅዕኖ ግምገማ መመሪያ ቁጥር 001/2010 ክፍል 3 የቀጠለ…..
1.1 የአካባቢ ክትትል/ምርመራ እቅድ
ይህ ክፍል ዝርዝር የአካባቢ ክትትል እቅድ የሚቀርብበት ክፍል ሲሆን የተጽእኖ ማቃለያ ተግባራት በአግባቡ መከናወናቸውን ለማረጋገጥ የሚዘጋጅ የእቅድ አካል ነው፡፡ በዚህ መመሪያ መሰረት በምድብ አንድ ስር ለተካተቱ ትልልቅ ፕሮጀክቶች የፕሮጀክቱ ባለቤት ቋሚ የውስጥ የአካባበቢ ክትትል ባለሙያ የመቅጠር ግደታ አለበት፡፡ ሁሉም ፕሮጀክቶች የአካባቢ አያያዝ እቅድ አተገባበራቸውን በዓመት ሁለት ጊዜ በየደረጃው ላለ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም ሪፖርት ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡ የአካባቢ ክትትል እቅዱ ፎርማት በእዝል 15.2 ቀርቧል፡፡ የአካባቢ ተፅዕኖ ዘገባ ተገምግሞ ከጸደቀ በኋላ የፕሮጀክት የዲዛይን ለዉጥ ከተከሰተና የተወሰኑ ዝርዝር ተግባራት ከተቀየሩ፤ እነዚህ ለውጦች ለሚመለከተው የአካባቢ ጥበቃ መስሪያ ቤት መቅረብና መፅደቅ ይኖርባቸዋል፡፡ ይህ እቅድ የሚከተሉትን አንኳር ነጥቦች ሊይዝ ይገባል፡፡
1) ክትትል የሚደረግባቸው የማቃለያ ተግባራት ዝርዝር
2) ክትትሉን የሚያደርገው ተቋም
3) ክትትሉን የሚያደርገው ተቋም የክትትል ስራውን ለማከናወን የሚጠቀምባቸው ዘዴዎች/ስልቶች፣
4) ክትትል የሚደረግባቸው የተግባራት አመላካቾችና ጥቅም ላይ የሚዉሉ ደረጃዎች (ስታንዳርድ) ወይም የአሰራር መመሪያዎች፣
5) ክትትል የሚካሄድበት የድርጊት መርሃ ግብር፣
1.2 በፕሮጀክቱ ትግበራ ተጽእኖ የሚደርስባቸውና የሚመለከታቸው አካላት ምክክር ማካሄድ
የአካባቢ ተጽእኖ ግመገማ ሪፖርት ለማዘጋጀት መካሄድ ካለባቸው ተግባራት መካከል በፕሮጀክቱ ትግበራ ተጽእኖ የሚደርስባቸውና የሚመለከታቸው አካላት በጥናት ሂደቱ ውስጥ ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ማወያየት ሲሆን በተለይም በወሰን ልየታና በረቂቅ የአካባቢ ተጽእኖ ሪፖርቱ ላይ የሚካሄዱ ውይይቶች ወሳኝ ናቸው፡፡ በረቂቅ ሰነዱ ላይ ውይይት ሲደረግ በፕሮጀክቱ ተጎጂ ወይም ተጠቃሚ የሚሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎች፣ በየደረጃው ያሉ የአካባቢ ጥበቃ ተቋማትና የሚመለከታቸዉ አጋር አካላት መገኘት ይኖርባቸዋል፡፡ ፕሮጀክቱ በሚተገበርበት ቀበሌ/ወረዳ ውስጥ ያሉ አመራሮች፣ ፕሮጀክቱ የሚተገበርበት ጎጥ መሪዎች፣ የሴቶች/የወጣቶች ተወካዮች፣ በፕሮጀክቱ ምክንያት በቀጥታ ጉዳት የሚደርስባቸዉ የህብረተሰብ ክፍሎች መሳተፍ አለባቸዉ፡፡ የውይይት ተሳታፊዎች በአበይት ተጽእኖዎች፣ በማቃለያ እርምጃዎችና በአካባቢ አያያዝ እቅዱ ትግበራ ላይ በዝርዝር መወያየትና ስምምነት ላይ መድረስ አለባቸዉ፡፡ ሀሰተኛ የማህበረሰብ ውይይት ማስረጃ የሚያያይዝ አማካሪ ድርጅት (የፕሮጀክት ባለቤት) ሰነዱ ሀሰተኛ መሆኑ ከተረጋገጠ በማንኛውም ጊዜ አግባብ ባለው ህግ መሰረት ተጠያቂ መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ የተሰጠው የአካባቢ ይሁንታ ፍቃድ ወዲያውኑ የሚሰረዝ ይሆናል፡፡ የተካሄደው ውይይት ሪፖርት የሚከተሉትን ነጥቦች ማካተት ይኖርበታል፤
1) ውይይቱ የተካሄደበት ጊዜ፣ በውይይቱ የተገኙ የማህበረሰብ ክፍሎች ከለር ፎቶግራፎች፣እንዳስፈላጊነቱ የድምጽና የተንቀሳቃሽ ምስል እንዲያቀርብ ሊደረግ ይችላል፡፡
2) ውይይቱ የተካሄደበት መንገድ ወይም ዘዴ
3) በውይይቱ የተነሱ ስጋቶች/ጥያቄዎች እና የተሰጡ ምላሾች እንዲሁም የማህበረሰቡ የስምምነት ሁኔታ፣
4) የሚመለከታቸው ተሳታፊዎች ስም ዝርዝርና ፊርማ የያዘና ፕሮጀክቱ በሚተገበርበት ወረዳ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም ኃላፊ የተፈረመና በማህተም የተረጋገጠ የውይይቱ ቃለ ጉባኤ፣
1.3 ማጠቃለያና ምክረ-ሃሳብ
ይህ ክፍል ውሳኔ ለመስጠት የሚያስችሉ ዋና ዋና ጉዳዮችን በአጭሩ ለማስገንዘብ የሚረዳ የተጽዕኖ ዘገባ ክፍል ነው፡፡ በዚህ ክፍል እንዲተገበሩ የተመረጡ አማራጮችና የተመረጡበት ምክንያት በዝርዝር መገለፅ ይኖርበታል፡፡ ሊወገዱ የማይችሉ አሉታዊ ተፅእኖዎችን ለማካካስ ወይም ተያያዥ የሆኑ ስጋቶችን ለመቀነስ የምንጠቀማቸውን ስልቶች በዝርዝር ማሳየት ይጠበቅበታል፡፡ በአጠቃላይ ይህ ክፍል የሚከተሉትን መረጃዎች ማካተት አለበት፡፡
1) የቁልፍ ጉዳዮች ግልጽ ማብራሪያ
2) ጉልህ የሆኑ አሉታዊ ተፅእኖዎችን ለመቀነስ ወይም ለማካካስ የሚወሰዱ እርምጃዎች
3) አዎንታዊና አሉታዊ ተፅእኖዎችን በማመዛዘን የፕሮጀክቱን አዋጭነት
4) ሊተኩ የማይችሉ የአካባቢ ሃብቶችን የሚጠቀም/ የሚያጠፋ መሆኑና አለመሆኑ
5) ለክትትልና ቁጥጥር ስራዎች የሚያስፈልጉ የህግ ማዕቀፎችና ሌሎች ወሳኝ የሆኑ ሃሳቦች ሊቀርቡ ይችላሉ፡፡
1.4 ዋቢ መፃህፍት/ማጣቀሻዎች
ይህ ክፍል በሪፖርቱ ውስጥ የተጠቀምንባቸውን መጻህፍቶች፣ የጥናት ሪፖርቶች፣ ድረ-ገፆች ወዘተ.. የሚገለጽበት ክፍል ነው፡፡ ለመረጃነት ጥቅም ላይ የዋሉ የማጣቀሻ ምንጮች ዓለም አቀፍ የአፃፃፍ ስልቶችን በመጠቀም በፅሁፎች ውስጥና በመጨረሻም ራሱን ችሎ በዚህ ክፍል መቀመጥ ይኖርበታል፡፡
1.5 እዝሎች
በዚህ ክፍል የሚያያዙት መረጃዎች ለገምጋሚው አካል እንደማጣቀሻነት የሚያገለግሉ ስለሆኑ ተለይተው በዋናው የጥናት ዘገባ ሰነድ መጨረሻ ላይ ይያያዛሉ፡፡ እነዚህ ሰነዶች ገምጋሚው አካል ትክክለኛ ውሳኔ ላይ እንዲደርስ የሚያስችሉ ናቸው፡፡ በእዝል ላይ መያያዝ የሚገባቸው መረጃዎች፤
1) የምህፃረ-ቃላት ፍችና የቃላት ትርጉም፣
2) ከሚመለከታቸው የአካባቢ ጥበቃ መ/ቤቶች ወይም ከአካባቢው አስተዳደሮች የተሰጡ የድጋፍ ደብዳቤዎች፣
3) የደህንነት ወይም የምርት ጥራት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት፣ የጤና እና የምርት ጥራት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት (ካስፈለገ)፣
4) ጥልቀት ያላቸው ቴክኒካል ሪፖርቶች፣ አመላካች ቻርቶችና የቦታው ካርታ፣
5) የህብረተሰቡን ተሳትፎ የሚገልጹና የፀደቁ ቃለ-ጉባኤዎች፣ በውይይት የተሳተፉ ሰዎች ፎቶግራፎች፣
6) የጥናት ቡድኑ አባላት ዝርዝር መረጃ (ስም፣ ግለ-ታሪክ ወዘተ)፣
7) ጥናቱን ያካሄደው አማካሪ ድርጅት የሙያና ንግድ ፈቃዶች፣
😎 የፕሮጀክቱ ባለቤት ስለ ጥናት ሰነዱ ትክክለኛነት የሰጠው ማረጋገጫ፣
9) በቀረበው የመጀመሪያ ረቂቅ የተጽዕኖ ጥናት ዘገባ ላይ በገምጋሚ ባለሙያዎች የተሰጡ አስተያየቶች ቅጅ እና ሌሎችም ካሉ ሊያያዙ ይገባል፡፡
1.6 የነባርና ማስፋፊያ ፕሮጀክት የአካባቢ አያያዝ እቅድ ዝግጅት
በዚህ አንቀጽ ንዑስ አንቀጽ 5.1 እስከ 5.17 የተዘረዘሩት የአካባቢ ተጽዕኖ ግምገማ ሪፖርት ዝግጅት ቅደም ተከተሎች በሙሉ ለአካባቢ አያያዝ እቅድ ዝግጅት የሚያገለግሉ ይሆናሉ፡፡ ይሁን እንጅ የአካባቢ አያያዝ እቅድ የሚዘጋጀው ወደፊት የሚፈጠሩ ችግሮችን (ተጽዕኖዎችን) በመተንበይ ብቻ ሳይሆን በአካባቢ ተጽዕኖ ግምገማ ትንተና ወቅት በተጨባጭ እየተከሰቱ ያሉትን ችግሮችና የችግሮችን የተጽዕኖ ደረጃ በመለየትና የማቃለያ እርምጃ በማዘጋጀት ይሆናል፡፡ የአካባቢ አያያዝ እቅዱ ሲዘጋጅ ከሌሎች መረጃዎች በተጨማሪ የአካባቢ ምርመራ በማካሄድና የምርመራ ሪፖርቱን በግብዓትነት በመጠቀም ይሆናል፡፡ ከአካባቢ ተጽዕኖ ግምገማ ሪፖርት ዝግጅት በተመሳሳይ በጥናት ከተለዩ የተጽዕኖ ማቃለያ እርምጃዎች በመነሳት የአካባቢ አያያዝ እቅዱ የሚዘጋጅ ይሆናል፡፡
2 የአካባቢ ተጽዕኖ ግምገማ ሪፖርትን ስለመገምገም
2.1 በአካባቢ ተጽዕኖ ግምገማ ሪፖርት ግምገማ ወቅት ትኩረት የሚደረግባቸው ጉዳዮች
1) የአካባቢ ተጽእኖ ግምገማ ሪፖርት ግምገማ በተዘጋጀው ቢጋር መሰረት መካሄዱን፣ የማህበረሰቡ አስተያየት መካተቱን፣ ውሳኔ ለመስጠት የሚያስችል በቂና የተሟላ መረጃ የያዘ መሆኑን ለማረጋገጥ እና በሰነዱ ውስጥ ያሉ ክፍተቶችን (ጉድለቶችን) ለመለየት ነው፡፡ በኘሮጀክት ባለቤቶች የተዘጋጀው የአካባቢ ተፅእኖ ግምገማ ሪፖርት ስልጣን በተሰጠው የአካባቢ ጥበቃ ተቋም፣ በሚመለከታቸው ተቋማት፣ በኘሮጀክቱ ምክንያት ጉዳት በሚደርስባቸዉና አስተያየት ለመስጠት ፍላጐቱ ባላቸው የህብረተሰብ ክፍሎች ቀርቦ መገምገም ይኖርበታል፡፡
2) የሰነድ ግምገማው በሚካሄድበት ወቅት በገምጋሚው ትኩረት ተሰጥቶ መታየት ካለባቸው ጉዳዮች መካከል የሚከተሉት ዋነኞቹ ናቸው፡፡
1) ሪፖርቱ በተዘጋጀውና በጸደቀው ቢጋር (ToR) መሰረት ተጠንቶ የቀረበ መሆኑንና ቢጋሩ ተሻሽሎ ከሆነ የተሻሻለበትን ምክንያት በማጠቃለያና በመግቢያ ጽሁፉ ዉስጥ መጠቀሱን፣ የአካባቢ ወሰን ልየታ ጥናት ቀርቦ የፀደቀ ስለመሆኑ ከገምጋሚው አካል የተሰጠ ደብዳቤ ከጥናት ሰነዱ ጋር አባሪ ሆኖ መቅረቡን ማረጋገጥ፣
2) ማንኛዉም ሊያነብ የሚችል ሰዉ ሊረዳዉ የሚችል አጭር ማጠቃለያ ጽሁፍ መኖሩን፣
3) ለዋና ዋና የሪፖርቱ ክፍሎች ጠቃሚ፣ ትክክለኛና ተቀባይነት ያላቸው መረጃዎች መካተታቸውን፣
4) በሪፖርቱ መሰረታዊ የአካባቢ መረጃዎች በአግባቡ መካተታቸውን፣
5) የጥናቱ ግኝቶች የተሟሉና አጥጋቢ መሆናቸውን፣
6) መረጃው ለውሳኔ ሰጭ አካላትና ለሚመለከታቸው የማህበረሰብ ክፍሎች ግልጽና በቀላሉ የሚረዱት መሆኑን፣
7) ጉልህ አወንታዊና አሉታዊ ተጽእኖዎች በአግባቡ መለየታቸውንና መተንተናቸውን፣
😎 ጉልህ አሉታዊና አወንታዊ ተጽእኖዎች ላይ የተቀመጡ ሙያዊ ውሳኔዎች በአግባቡ መገለጻቸዉን፣
9) ፕሮጀክቱ ተግባራዊ ባይሆን የሚለዉን ጨምሮ ያሉ የተለያዩ የትግበራ አማራጮች በአግባቡ መዳሰሳቸውንና አማራጮችን በንጽጽር ለማየት የተጠቀሙባቸው መመዘኛዎች ለሁሉም አማራጮች በእኩል ክብደት የተሰጣቸው መሆኑን፣
10) ከፕሮጀክት አማራጮች መካከል ለአካባቢና ማህበራዊ ሁኔታዎች በአንጻራዊነት ተስማሚ የሆነዉ አማራጭ መመረጡንና የተመረጠበትም ምክንያት በአግባቡ መገለጹን፣
11) አጋር መ/ቤቶች፣ ጉዳት ሊደርስባቸዉ ይችላል ተብሎ የሚገመቱና በፕሮጀክቱ ላይ አስተያየት ለመስጠት ፍላጎቱ ያላቸዉ የህብረተሰብ ክፍሎች በአግባቡ መሳተፋቸዉን የሚገልጽ ማስረጃ በአካባቢ ተፅዕኖ ግምገማ ሪፖርት ዉስጥ መኖሩን ፣
12) በጥናቱ ወቅት ለመረጃ ምንጨነት ያገለገሉት ማጣቀሻዎች በአግባቡ መገለጻቸውን፣
13) ሊደርሱ የሚችሉ ተጽእኖዎችን ለመተንበይና ለመለየት ጥቅም ላይ የዋሉ ዘዴዎችና ቀመሮች እንዲሁም እያንዳንዱን አሉታዊ ተጽእኖ ለማቃለል የተቀመጡ እርምጃዎች በአግባቡ መገለጻቸዉን እና ያጋጠሙ የመረጃ ክፍተቶች መታየታቸዉን፣
14) የአካባቢ አያያዝና ክትትል እቅዱ ሊለካ የሚችል፣ የሚያስፈልገዉ ወጪ፣ ጊዜና ስራዉን የሚያከናውን ተቋም/ አካል በዘገባው ዉስጥ መካተቱን፣
15) በአጠቃላይ መረጃው ስለፕሮጀክቱ ትግበራ ውሳኔ ለመስጠት ጠቃሚና በቂ መሆኑን፣
16) የሚቀርበው የጥናት ዘገባ የታደሰ የሙያ ፈቃድና የንግድ ፈቃድ እንዲሁም የአማካሪ ድርጅቱ የሙያ ፈቃድ፤ የጥናት ቡድኑ የባለሙያዎች ስብጥርና በጥናቱ የተሳተፉበት የጥናት ክፍልና በጥናቱ ስለመሳተፋቸው የማረጋገጫ ሰነድ፣ የታደሰ የብቃት ማረጋገጫ ሰርተፊኬት፣ በባለሙያዎች ፊርማ የተረጋገጠ የባለሙያዎች ግለ-ታሪክ፣ በፎቶግራፍ የተደገፈ የማህበረሰብ ተሳትፎ/ውይይት ቃለጉባኤ፣ የአካባቢው የመንግስት አካል ስለፕሮጀክቱ ትግበራ የተስማማበት የድጋፍ ደብዳቤ መያያዙን፣
17) ለግምገማ የቀረበው ሪፖርት የፕሮጀክት ባለቤቱና የአማካሪ ድርጅቱ ማህተም በእያንዳንዱ ገፅ ላይ ያረፈበት መሆኑን፣ በአሳማኝ ምክንያት ባለሀብቱ ማህተም ማድረግ ካልቻለ የአማካሪ ድርጅቱ ማህተም በቂ ሊሆን ይችላል፡፡ የይሁንታ ፈቃድ ይሰጠኝ ከሚለው ማመልከቻ ላይ የፕሮጀክት ባለቤቱ ወይም የተወካዩ ፊርማና ማህተም ያለበት መሆኑን ማረጋገጥ ይገባል፣
3) የአካባቢ ተጽዕኖ ግምገማ ባለሙያዉ/ቡድኑ ከላይ በንዑስ አንቀጽ 6.1 ስር በተራ ቁጥር 2 በተዘረዘሩት አስራ ሰባት የመገምገሚያ ነጥቦች መሰረት በመገምገም የተጽዕኖ ዘገባውን ዝርዝር የግምገማ ሪፖርትና አጠቃላይ የፕሮጀክቱን ትግበራ የውሳኔ አስተያየት ለኃላፊዎች ይቀርባል፡፡ በቀረበው የውሳኔ አስተያየት ተመስርተው ኃላፊዎች ውሳኔ ይሰጣሉ፡፡ ኃላፊው የአካባቢ ተጽእኖ ጥናት ዘገባው ዝርዝር ጥናት ጎድሎታል ብሎ ካመነ ወይንም የቴክኒክ ችግር አለበት ብሎ ከገመገመ መሰረዝ ወይንም እንደገና እንዲጠና ሊያዝዝ ይችላል፡፡
4) በፕሮጀክት ባለቤቶች ተጠንቶ የሚቀርበዉን የፕሮጀክቶች የአካባቢ ተጽእኖ ግምገማ ሪፖርት ለመገምገም የሚያገለግሉ መመዘኛዎች በእዝል 15.3 በሰንጠረዥ ተዘርዝረዋል፡፡ ስለዚህ ማንኛውም የአካባቢ ተጽዕኖ ግምገማ ሪፖርት በዚህ መመዘኛ መሰረት መገምገም አለበት፡፡ በየደረጃዉ ያሉ የአካባቢ ጥበቃ ተቋማት የቀረበላቸውን የአካባቢ ተፅእኖ ጥናት ዘገባ በ15 ቀናት ውስጥ መርምረው ምላሽ መስጠት አለባቸው፡፡ ነገር ግን ፕሮጀክቱ በጣም ጉልህ የሆኑ ችግሮችን የሚያስከትል ከሆነ ምላሽ የሚሰጥበት ቀን ከ15 ቀናት በላይ ሊዘገይ ይችላል፡፡ ነገር ግን ምለሽ የሚሰጥበት ጊዜ ከ30 ቀን መብለጥ የለበትም፡፡ የግምገማ ሥራው እንደተጠናቀቀ የባለስልጣኑ መስሪያ ቤት ወይም የሚመለከተው በተዋረድ ያለ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም ጥናቱን እንዳለ ሊቀበለው፣ ሊሰርዘው ወይም እንዲስተካከል ሊያዝዝ ይችላል፡፡ የአካባቢ ተጽእኖ ግምገማ ሪፖርቱን ለመገምገም በአካባቢ ጥበቃ ተቋም ባሉ ሙያተኞች ብቻ መገምገሙ በቂ ነው ብሎ ካልታመነበት የተቋሙ የበላይ ሀላፊ ሰነዱ በዩኒቨርሲቲዎች፣ በምርምር ተቋማትና በሌሎች የሚመለከታቸው ተቋማት እንዲገመገም ሊያዝዝ ይችላል፡፡
የአካባቢ ተጽእኖ ግምገማ ሪፖርት ተቀባይነት ላይ ውሳኔ ስለመስጠት
በዕዝል 15.3 የቀረበውን የመገምገሚያ መስፈርት በመጠቀም የአካባቢ ተጽዕኖ ግምገማ ሪፖርቱ ተገምግሞ ነጥብ ይሰጠዋል፤ የነጥቡ ክብደት አጠቃላይ 100 ፐርሰንት ሲሆን በሰነዱ ውስጥ አስፈላጊ መረጃዎች ስለመኖራቸው ከ56% እና ሰነዱ ለያዛቸው መረጃዎች በቂነት ከ44% ነጥብ ይሰጣል፡፡
1) በሰነድ ግምገማው የተገኘው ነጥብ አጠቃላይ ውጤቱ 70 ፐርሰንት ወይም በላይ ከሆነ የአካባቢ ይሁንታ ሰርተፊኬት ተዘጋጅቶ ይሰጠዋል፡፡ ለባለሃብቱ የሚሰጠው የይሁንታ ፈቃድ በዕዝል 15.9 ላይ የተዘረዘሩትን የውል ስምምነቶችን ያካተተ ይሆናል፡፡
2) የተሰጠው ነጥብ በ50 እና በ70 ፐርሰንት መካከል ከሆነ ሰነዱ እንደገና ተስተካክሎ እንዲቀርብ ነጥብ የተሰጠበትን መገምገሚያ ቅፅ አባሪ በማድረግ ለፕሮጀክት ባለቤቱ በደብዳቤ ይገለጽለታል፡፡
3) የግምገማ ነጥቡ ከ50 ፐርሰንት በታች ከሆነ የቀረበው ዘገባ ተቀባይነት የሌለው ወይም ጥራት የጎደለው በመሆኑ በሌላ አማካሪ ድርጅት ተዘጋጅቶ እንደገና እንዲቀርብ በመግለፅ ነጥብ የተሞላበትን የመገምገሚያ ቅፅ አባሪ በማድረግ በደብዳቤ ለፕሮጀክት ባለቤቱ ይገለጽለታል፡፡
4) የአካባቢ ተጽዕኖ ግምገማ ሪፖርት የያዘው መረጃ በቂና ትክክለኛ መሆኑን ሳያረጋገጥ የይሁንታ ፈቃድ እንዲሰጠው የውሳኔ ሀሳብ ያቀረበ ባለሙያ ወይንም በመስክ መረጋገጥ ያለባቸውን መረጃዎች በአግባቡ ሳያረጋግጥ መተግበር በሌለበት ቦታ ላይ እንዲተገበር የውሳኔ አስተያየት ያቀረበ ባለሙያ በዲሲፕሊን መመሪያው መጠየቁ እንደተጠበቀ ሆኖ አግባብ ባላቸው በሀገሪቱ ህጎች ይጠየቃል፡፡
2.2 ስለ አካባቢ ይሁንታ ፈቃድ የአገልግሎት ክፍያ ታሪፍ
የፕሮጀክቶች የይሁንታ ፈቃድ አሰጣጥ ሂደት የባለሙያ የመስክ ስምሪትን የሚጠይቅ በመሆኑ አገልግሎቱ የመንግስትን ወጭ ይጠይቃል፡፡ የአካባቢ ተጽዕኖ ግምገማ የአገልግሎት ሙሉ ወጭ በባለሀብቱ እንዲሸፈን በህግ ቢደነገግም እስካሁን ድረስ በመንግስት በጀት ሲሸፈን መቆየቱ ይታወቃል፡፡ በዚህ ከቀጠለ ደግሞ በመንግስት በጀት ላይ ጫና መፍጠሩ አይቀርም፡፡ በመሆኑም በአካባቢ ተጽዕኖ ግምገማ አዋጆች ቁጥር 181/2003 አንቀጽ 9/4 መሰረት የፕሮጀክት ባለቤቶች ሙሉ የአካባቢ ተጽዕኖ ወጭዎችን የመሸፈን ግደታ ያለባቸው ቢሆንም ለጊዜው በተወሰነ ደረጃ የአገልግሎት ወጭ እንዲሸፍኑ በዚህ መመሪያ ተደንግጓል፡፡ ክፍያ የሚከፈልባቸው የአገልግሎት አይነቶችና የክፍያ መጠን ቀጥሎ በቀረበው ሰንጠረዥ መሰረት የሚፈጸም ይሆናል፡፡ የይሁንታ ፈቃድ ከመሰጠቱ በፊት የአገልግሎት ክፍያ የተፈጸመበት ደረሰኝ ፎቶ ኮፒ ከውሳኔ አስተያየት ሪፖርቱ ጋር ተያይዞ መቅረብ ይኖርበታል፡፡
ሰንጠረዥ 1: የአካባቢ ይሁንታ ፈቃድ ለመስጠት፣ ለማደስ ወይም ለመተካት የሚከፈል የአገልግሎት ክፍያ
ተ/ቁ የአገልግሎት አይነት መለኪያ የአገልግሎት ክፍያ በፕሮጀክት ምድብ
የክልል የዞን የወረዳ
1 አዲስ ይሁንታ ፈቃድ መስጠት ብር ክልል 1000 የዞን 500 ወረዳ 250
2 በወቅቱ ለቀረበ የእድሳት ጥያቄ ብር ክልል 500 የዞን250 ወረዳ150
3 በልዩ ልዩ ሁኔታ የጠፋና የተበላሸ የይሁንታ ፈቃድ ለመተካት (በወቅቱ ለቀረበ) ብር ክልል 600 የዞን 400 ወረዳ 200
4 በወቅቱ ላልቀረበ የእድሳት ጥያቄ (የእድሳት ጊዜው ከ6 ወራት በላይ ካላለፈ)
ብር ክልል 600 የዞን400 ወረዳ 200
5 በወቅቱ ላልቀረበ የእድሳት ጥያቄ (የእድሳት ጊዜው ከ 1 አመት በላይ ካላለፈ)
ብር ክልል 1000 የዞን500 ወረዳ 300
6 በወቅቱ ላልቀረበ የእድሳት ጥያቄ (የእድሳት ጊዜው ከ 2 አመት በላይ ካላለፈ)
ብር ክልል 1200 የዞን700 ወረዳ 400
7 የጠፋና የተበላሸ የፕሮጀክት የይሁንት ፈቃድ መተካት (የእድሳት ጊዜው ከ6 ወራት በላይ ካላለፈ) ብር ክልል 1000 የዞን 500 ወረዳ 300
8 የጠፋና የተበላሸ የፕሮጀክት የይሁንታ ፈቃድ መተካት (የእድሳት ጊዜው ከ1 ዓመት በላይ ካላለፈ) ብር ክልል 1200 የዞን700 ወረዳ 500
9 የጠፋና የተበላሸ የፕሮጀክት የይሁንታ ፈቃድ መተካት (የእድሳት ጊዜው ከ2 ዓመት በላይ ካላለፈ) ብር ክልል 1400 የዞን900 ወረዳ 700
10 በወቅቱ ላልቀረበ የይተካልኝና የእድሳት ጥያቄ (የእድሳት ጊዜው ከ 2 አመት በላይ ካላፈ)
እንደገና አዲስ የተጠና ሪፖርት እንዲያቀርብ ይገደዳል እንጂ አይታደስም
3 የፕሮጀክት ትግበራ ስለሚከለከልባቸዉና ስለሚሰረዝባቸው አግባቦች
አንድ ፕሮጀክት ቢተገበር/ሲተገበር የሚያስከትለው አሉታዊ ተጽዕኖ ከፍተኛ ከሆነና ተጽዕኖውን በአጥጋቢ ሆኔታ ማስቀረት የማይቻል ከሆነ ወይም ተጽዕኖውን ለማስቀረት እንደማይቻል ከታመነ ሌላ አማራጭ ቦታ እንዲፈልግ ወይም ቴክኖሎጂ እንዲጠቀም ይደረጋል፡፡ ስለዚህ ይህ ክፍል የፕሮጀክቱ ትግበራ የሚከለከልባቸውን (የሚቋረጥበትን) አግባቦች ለመወሰን ያስችላል፡፡ የአንድ ፕሮጀክት ትግበራ የሚከለከለው፡-
1) ሁለት የማይጣጣሙ ፕሮጀክቶች ጎን ለጎን ተግባራዊ እንዲሆኑ የአካባቢ ተጽዕኖ ጥናት ዘገባ የቀረበ ከሆነና በኋላ የቀረበዉ ፕሮጀክት ቀድሞ ከቀረበው ፕሮጀክት ጋር የማይጣጣም ከሆነ የማይጣጣምበትን አሉታዊ ተጽዕኖዎች በመግለፅ ለፕሮጀክት ባለቤቱ ሌላ አማራጭ ቦታ እንዲፈልግ (የፕሮጀክቱን አይነት እንዲለውጥ) በደብዳቤ የሚገለፅለት ሲሆን ፕሮጀክቱ በማይጣጣምበት ቦታ እንዳይተገበር ይከለከላል፡፡
ይቀጥላል....................

18/03/2022

የቀጠለ…. የአካባቢ ተፅዕኖ ግምገማ መመሪያ ቁጥር 001/2010
ክፍል 4
1) የፕሮጀክቱ ተዳማሪ ተጽዕኖ በጣም ከፍተኛ ከሆነና አካባቢው ተጽዕኖውን መሸከም የማይችል ከሆነ ለአካባቢው ቅድሚያ በመስጠት ፕሮጀክቱ እንዳይተገበር ይከለከላል፡፡
2) ፕሮጀክቱ ሊተገበር በታቀደበት ቦታ ወይም አካባቢ ላይ በማህበረሰቡ ዘንድ ፕሮጀክቱ እንዳይተገበር ከፍተኛ ተቃውሞ ከገጠመ ተቃውሞው እስኪፈታ ለፕሮጀክቱ የአካባቢ ይሁንታ ፈቃድ አይሰጥም፡፡
3) ፕሮጀክቱ ሊተገበር የታሰበበት ቦታ በተለያዩ አካላት የይገባኛል ጥያቄ ውዝግብ ያለበት ከሆነና ውዝግቡ ካልተፈታ የአካባቢ ይሁንታ ፈቃድ አይሰጥም፡፡
4) ክልላዊና ሀገራዊ ቅርሶችን፣ ጥብቅ ቦታዎችን፣ ሃይማኖታዊና ባህላዊ ቦታዎችን፣ ታሪካዊ ሃብቶችን፣ እንዲሁም ሌሎች በቀላሉ ለጉዳት ተጋላጭ የሆኑ ቦታዎችን ፕሮጀክቱ በቀጥታ የሚነካ ከሆነና አማራጭ የማይገኝለት ከሆነ የአካባቢ ይሁንታ ፈቃድ አይሰጥም፡፡
5) ፕሮጀክቱ የሚጠቀምባቸው ቴክኖሎጂዎች በአካባቢ ጥበቃ ህጎች የተቀመጡትን የልቀት ደረጃዎች ሊያሟሉ የማይችሉ ከሆኑና ፕሮጀክቱ ከፍተኛ ልቀት የሚያስከትል ሆኖ ሲገኝ እንዲሁም የተከለከሉ ግብዓቶችን የሚጠቀም ከሆነ የአካባቢ ይሁንታ ፈቃድ አይሰጥም፡፡
6) ማንኛውም በአለም ባንክ በጀት ድጋፍ የሚደገፍ ፕሮጀክት ከዓለም ባንክ ፖሊሲ ወይም የህግ ማዕቀፎች ጋር የሚቃረን ወይም በባንኩ እንዲተገበር የማይፈቀድ ከሆነ የአካባቢ ይሁንታ ፈቃድ አይሰጥም፡፡
7) ከላይ በአንቀጽ 7 ንዑስ አንቀጽ 1 እስከ 7 የተጠቀሱትን የፕሮጀክት ትግበራ ክልከላዎች በመተላለፍ ወደ ተግባር የገባ ማንኛውም ፕሮጀክት ብር 100,000.00 (አንድ መቶ ሽህ ብር) ተቀጥቶ ፕሮጀክቱ እንዲዘጋ ወይም በራሱ ወጭ ወደ ሌላ ቦታ እንዲዛወር ይደረጋል፡፡
😎 በምድብ አንድና ሁለት ውስጥ ለተካተቱ ፕሮጀክቶች የአካባቢና ማህበራዊ ተጽዕኖ ማቃለያ እቅድ ሳያዘጋጁና የአካባቢ ይሁንታ ፈቃድ ሳይሰጣቸው፤ የአዘጋጁትም ቢሆኑ የተጽዕኖ ማቃለያ እቅዳቸው በፕሮጀክቱ ግንባታና ትግበራ ዲዛይን ውስጥ ሳይካተት ለፕሮጀክቶች የግንባታ ፈቃድ የሚሰጥ በየደረጃው ያለ የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ወይም ኢንዱስትሪና ኢንቨስትምንት ቢሮ ኃላፊ ወይም ባለሙያ በብር 50,000.00 (በሀምሳ ሺህ ብር) ወይንም በአምስት አመት ጽኑ እስራት ወይም በሁለቱም ይቀጣል፡፡
9) በምድብ አንድና ሁለት ውስጥ ለተካተቱ ፕሮጀክቶች የአካባቢና ማህበራዊ ተጽዕኖ ማቃለያ እቅድ ሳያዘጋጁና የአካባቢ ይሁንታ ፈቃድ ሳይሰጣቸው፤ የአዘጋጁትም ቢሆኑ የተጽዕኖ ማቃለያ እቅዳቸው በፕሮጀክቱ ግንባታና ትግበራ ዲዛይን ውስጥ ሳይካተት ለፕሮጀክቶች የስራ ፈቃድ የሚሰጥ የማንኛውም መስሪያ ቤት/ ድርጅት ኃላፊ/ባለሙያ በብር 50,000.00 (በሀምሳ ሽህ ብር) ወይንም በአምስት አመት ጽኑ እስራት ወይም በሁለቱም ይቀጣል፡፡
10) በየደረጃዉ ካሉ የአካባቢ ጥበቃ ተቋማት የይሁንታ ፈቃድ ሳይሰጠዉ ወደ ተግባር የገባ ማንኛውም ፕሮጀክት አሉታዊ አካባቢያዊና ማህበራዊ ተጽዕኖ ካለው ብር 50,000.00 (ሀምሳ ሽህ ብር) ተቀጥቶ ፕሮጀክቱ በሶስት ወራት ጊዜ ውስጥ የአያያዝ እቅድ አዘጋጅቶ እንዲያቀርብ ይገለጽለታል፤ በተቀመጠው የጊዜ ሰሌዳ ውስጥ ዘገባውን ማቅረብ ካልቻለ ስራውን እንዲያቆም ይደረጋል፣
11) በአካባቢና በሰዉ ጤና ላይ ተጽዕኖ እያስከተለ ያለ ፕሮጀክት ከሆነና ይህንኑ ለመከላከል አለመቻሉ በባለስልጣኑ መስሪያ ቤት ወይም በተዋረድ ባለ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም በምርመራ የተረጋገጠ ከሆነ የፕሮጀክቱ ይሁንታ እንዲሰረዝ (ስራውን እንዲያቆም) ይደረጋል፣
12) የፕሮጀክቱ ባለቤት የተጽእኖ ማቃለያ እርምጃዎችን ካልተገበረ እና በተሰጠው ግብረ መልስ መሰረት ተግባራዊ የማያደርግ ከሆነ ባለስልጣኑ ወይም በሚመለከተው በተዋረድ ያለ የአካባቢ ጥበቃ መስሪያ ቤት ብር 50,000.00 (ሀምሳ ሽህ ብር) ተቀጥቶ የጹሁፍ ማስጠንቀቂያ ይሰጠዋል፡፡ በተሰጠው ማስጠንቀቂያ መሠረት የኘሮጀክቱ ባለቤት ችግሩን የማያስተካክል ከሆነ ባለሥልጣኑ ወይም የሚመለከታቸው በተዋረድ ያለ የአካባቢ ጥበቃ መስሪያ ቤት የሰጠውን የይሁንታ ፈቃድ ያግዳል ወይም ይሰርዛል፡፡ ሌሎችም ፈቃድ ሰጭ መስሪያ ቤቶች ለኘሮጀክቱ ትግበራ የሰጡትን የስራ ፈቃድ ይህን ውሣኔ ተከትለው ማገድ ወይም መሠረዝ አለባቸው፡፡
13) በአዋጅ ቁጥር 181/2003 ዓ.ም አንቀፅ 15 (5) መሰረት የፕሮጀክት ባለቤቱ የአካባቢ ተቆጣጣሪዎችን ክትትል፣ ምርመራና ቁጥጥር እንዳያካሄዱ ወይም ወደ ፕሮጀክቱ ግቢ እንዳይገቡ የከለከለ እንደሆነ ብር 30‚000.00 (ሰላሳ ሽህ ብር) ተቀጥቶ የመጨረሻ የፅሁፍ ማስጠንቀቂያ ይሰጠዋል፤ የተሰጠውን ማስጠንቀቂያ ባለማክበር ለሁለተኛ ጊዜ ክትትል፣ ምርመራና ቁጥጥር እንዳይካሄድ ወይም የአካባቢ ተቆጣጣሪዎችን ወደ ፕሮጀክቱ ቅጥር ግቢ እንዳይገቡ ከከለከለ ባለሥልጣኑ ወይም በተዋረድ ያሉ የአካባቢ ጥበቃ መስሪያ ቤቶች የሰጡትን የይሁንታ ፈቃድ ያግዳሉ ወይም ይሰርዛሉ፡፡ ሌሎችም ፈቃድ ሰጭ መስሪያ ቤቶችም ለኘሮጀክቱ ትግበራ የሰጡትን የስራ ፈቃድ ይህን ውሣኔ ተከትሎ ማገድ ወይም መሠረዝ አለባቸው፡፡
14) የፕሮጀክት ባለቤቱ ባቀረበው ጥናት መሰረት የአካባቢ አያያዝ ዕቅዱን ስለመተግበሩ በዓመት ሁለት ጊዜ ለሚመለከተው የባለስልጣኑ መስሪያ ቤት ወይንም በተዋረድ ላለ የአካባቢ ጥበቃ መስሪያ ቤት ሪፖርት ማቅረብ አለበት (የሪፖርት ማድረጊያ ቅፁ በዕዝል 15.4 ተያይዟል)፡፡ የአካባቢ አያያዝ ዕቅድ ትግበራውን በወቅቱ ሪፖርት የማያደርግ ከሆነ ማስጠንቀቂያ ይሰጠዋል፤ በተከታታይ ሶስት ጊዜ ለሚመለከተው የአካባቢ ጥበቃ መስሪያቤት የአፈጻጸም ሪፖርት ካላቀረበ የባለስልጣን መስሪያቤቱ ወይም በተዋረድ ያለ የአካባቢ ጥበቃ መስሪያቤት የሰጠውን የይሁንታ ሰርተፊኬት ያግዳል ወይም ይሰርዛል፡፡
15) ለፕሮጀክቱ ተደጋጋሚ የአካባቢ ክትትልና ምርመራ በማድረግ ችግሮችን እንዲያስተካክል ቢገለጽለትም ችግሩን አላስተካክልም በማለቱ የመጨረሻ የማስጠንቀቂያ ደብዳቤ ተጽፎ በተሰጠዉ የጊዜ ገደብ ዉስጥ ችግሩን ማስተካከል ያልቻለ ፕሮጀክት የማስተካከያ እርምጃዎች ተግባራዊ እስከሚደረጉ ድረስ ፕሮጀክቱ ስራዉን እንዲያቆም ይደረጋል፡፡
1 የአካባቢ ህግ ማስከበር ግብረ-ሀይል ስለማቋቋም፣ተግባርና ኃላፊነት
አብዛኞች የልማት ፕሮጀክቶች አደገኛ ቆሻሻቸውን በቀጥታ ወደ አካባቢ በመልቀቃቸው የተነሳ በምግብ ስራዓተ ሰንሰለት፣ በስርዓተ-ምህዳርና በሰዎች ላይ የማይቀለበስ ውስብስብ ችግር እያስከተለ ስለሆነ በአንቀጽ 7 ላይ በተገለጸው አግባብ ተጽዕኖውን ማስወገድ ካልተቻለ በአካባቢ ህግ ማስከበር ግብረ ሀይል አማካይነት የአካባቢ ህግ የማስከበር ስራ ይሰራል፡፡ በዚሁ አግባብ፡-
1) ፋብሪካዎችና የአገልግሎት ሰጭ ተቋማት ደረቅና ፍሳሽ ቆሻሻቸውን አክመውና የሀገሪቱን የቆሻሻ የልቀት ደረጃዎች ጠብቀው ማስወገድ አለባቸው፡፡ ፕሮጀክቶች አካባቢን ከመበከል እንዲታቀቡ ተደጋጋሚ ድጋፍ ተደርጎላቸው የአካባቢ ህግን ለማክበር ፈቃደኞች ካልሆኑ የአካባቢ ጥበቃ መስሪያ ቤት የፕሮጀክቱን የይሁንታ ፈቃድ ይሰርዛል፤ ይህን ተከትሎ የስራ ፈቃድ ስጭ ተቋማት የሰጡትን ፈቃድ ይሰርዛሉ፡፡ የአካባቢ ጥበቃ ግብረ ሀይልም የአካባቢ ህጉን ለማስከበር ፕሮጀክቱን ይዘጋል (እንዲቋረጥ) ያደርጋል፡፡
2) ከአካባቢ ጥበቃ መ/ቤት የሚቀርብለትን የምስልና የጽሁፍ ማስረጃ መሰረት በማድረግ የአካባቢ ህግ ማስከበር ግብረ ሀይል በአዋጅ ቁጥር 181/2003 አንቀጽ 15 መሰረት የመዝጋት (የማገድ) እርምጃ መወሰድ አለበት፡፡
3) ይህን አስተዳደራዊ እርምጃ (ውሳኔ) ተግባራዊ ለማድረግ ከሚመለከታቸው ተቋማት የተዋቀረ የአካባቢ ህግ አስከባሪ ግብረ ሀይል በዚህ መመሪያ ተቋቁሟል፡፡
4) ግብረ-ሀይሉ በክልል ደረጃ የሚከተሉትን ተቋማት በአባልነት አቅፏል፡-
የግብረ-ሀይሉ አባል የሚሆኑ መስሪያ ቤቶች አባልነት
ከክልል ጠቅላይ አቃቤ ህግ መስሪያ ቤት የሚመደብ ሰብሳቢ
ከክልል ፖሊስ ኮሚሽን የሚመደብ አባል
ከክልል ጤና ጥበቃ ቢሮ የሚመደብ አባል
ከክልል ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ቢሮ የሚመደብ አባል
ከክልል የማዕድን ሀብት ልማት ማስፋፊያ ኤጀንሲ የሚመደብ አባል
ከክልል ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ የሚመደብ አባል
ከክልል ከተማ ልማት፣ ቤቶችና ኮንስትራክሽን ቢሮ የሚመደብ አባል
ከክልሉ አካባቢ ደንና ዱር እንስሳት ጥ/ልማት ባለስልጣን የሚመደብ ጸሀፊና አባል ይሆናሉ
5) ከዚህ በላይ የተቋቋመው ግብረ ሀይል የአካባቢ ደንና ዱር እንስሳት ጥበቃና ልማት ባለስልጣን የሚያቀርብለትን የአካባቢ ብክለትና ብክነት የምርመራና ክትትል ሪፖርት ማስረጃዎች እየመረመረና አስፈላጊም ሲሆን የመስክ ምልከታ እያደረገ በመረጃ ላይ የተመሰረተ እርምጃ ይወስዳል፡፡ እርምጃው ፕሮጀክቶችን ለተወሰነ ጊዜ መዝጋት ወይንም መሰረዝ ሊሆን ይችላል፡፡
6) የአካባቢ ጥበቃ ግብረ ሀይል በዚህ መመሪያ መሰረት በየደረጃው ባሉ የዞንና የወረዳ አደረጃጀቶች የተቋቋመ ሲሆን ተግባርና ኃላፊነቱንም በዚህ አንቀጽ በተገለጸው አግባብ ይወጣል፡፡
2 ለአካባቢ አማካሪ ድርጅቶችና ባለሙያዎች የአማካሪነት የሙያ ፈቃድ ስለመስጠት
ይህ ክፍል ባለስልጣኑ የአካባቢ አማካሪ ድርጅቶችንና አማካሪ ባለሙያዎችን የሙያ ፈቃድ ለመስጠት፣ አመልካቾች ማሟላት የሚገባቸዉን መስፈርቶችና ሰነዶች፣ የአማካሪዎችን ተግባርና ኃላፊነት የሚወስን ይሆናል፡፡
2.1 የአካባቢ ተጽዕኖ ዘገባ የማዘጋጀት ስልጣን
1) ለማንኛውም ፕሮጀክት የአካባቢ ተጽዕኖ ጥናት ዘገባ የሚዘጋጀዉ በዚህ መመሪያ ዉስጥ የተዘረዘሩ መስፈርቶችን በሚያሟሉ የባለሙያዎች ስብጥርና ህጋዊ ፈቃድ ባላቸው አማካሪ ድርጅቶች ብቻ ይሆናል፡፡ ነገር ግን የዓለም ባንክ ፕሮጀክቶችን በተመለከተ ሀገራችን ባፀደቀችው ህግ መሰረት ተፈፃሚ ይሆናል፡፡
2) የአካባቢ አማካሪነት የሙያ ፈቃድ ለማዉጣት የሚፈልግ ባለሙያ በዕዝል 15.5-15.7 ከተጠቀሱት የትምህርት ዝግጅቶች አንዱ ሊኖረዉ ይገባል፡፡ ለመጀመሪያ ዲግሪ አምስት ዓመትና በላይ የሥራ ልምድ፣ ለሁለተኛ ዲግሪ ሶስት ዓመትና በላይ የሥራ ልምድ እና ለሶስተኛ ዲግሪ ሁለት ዓመትና በላይ የሥራ ልምድ ያለው/ያላት መሆን አለበት፡፡
2.2 በአካባቢ አማካሪነት ስራ ለመሰማራት መሟላት የሚገባቸዉ መስፈርቶች
1) የታደሰ የሙያ ብቃት ማረጋገጫ ማስረጃ፣
2) በአማካሪ ድርጅት የተደራጁ መሆን አለባቸው፤
3) አንድ አማካሪ ድርጅት ፈቃድ ለማውጣት 6 የተለያዩ የሙያ ዘርፎችን ያካተቱ አማካሪ ባለሙያዎች መያዝ ያለበት ሲሆን ስድስቱም ባለሙያዎች የሙያ ብቃት ማረጋገጫ ያላቸው መሆን አለባቸው፣
4) በአንድ የአካባቢ ተጽዕኖ ጥናትና ዘገባ ዝግጅት ላይ የሚሳተፉ ባለሙያዎች ቁጥር ቢያንስ አራት ባለሙያዎች ሆኖ እንደ ፕሮጀክቱ ባህሪ የተለያየ የሙያ ስብጥር ያላቸው ሊሆኑ ይገባል፣
5) የባለሙያዎች ቁጥር እንደ ፕሮጀክቱ ባህሪ የሚለያይ ሆኖ በዝቅተኛው ቁጥር ላይ ያሉት አራቱም ባለሙያዎች የተለያየ የአማካሪነት የሙያ ብቃት ማረጋገጫ ሊኖራቸው ይገባል፣
6) የታደሰ የንግድ ስራ ፈቃድ፣
7) የታደሰ የአማካሪነት የድርጅት ፈቃድ፣
😎 የራሱ የሆነ የተሟላ ቋሚ ጽ/ቤት ያለው፣ ስራስኪያጅና ጸሀፊ ባለሙያ ያለው
9) መሰረታዊ የአካባቢ መረጃ መሰብሰቢያና መለኪያ መሳሪያዎችን (ጅፒኤስ፣ቪዲዮ ካሜራ፣ድጅታል ካሜራ፣ኮምፒውተር ወዘተ) ያሟላ መሆን ይኖርበታል
10) ለአማካሪ ባለሙያ የሙያ ብቃት እንዲሁም ለአማካሪ ድርጅት (firm) ፈቃድ የሚሰጠው በክልሉ አካባቢ ደንና ዱር እንስሳት ጥበቃና ልማት ባለስልጣን ብቻ ነው፡፡
11) አንድ ባለሙያ ከሁለት አማካሪ ድርጅቶች በላይ አማካሪ ሆኖ እንዲሰራ ወይም እንዲደራጅ አይፈቀድም፡፡
2.3 የሙያ ብቃት ማስረጃ በአዲስ ለማውጣትና ለዕድሣት አገልግሎት ክፍያ
1) የሙያ ብቃት ማረጋገጫ ስርቲፊኬት ወይም የአማካሪ ድርጅት ፈቃድ የሚታደሰው በዚህ መመሪያና በአካባቢ ህጎች የተካተቱ ህጎችና የሙያ ስነ ምግባሮች አፈጻጸም በምርመራ ከተረጋገጠ በኋላ ይሆናል፡፡
2) ባለሙያዎች አዲስ የሙያ ፈቃድ ለማዉጣት፣ ደረጃቸውን ለማሳደግና የጠፋባቸው በድጋሚ ለማዉጣት ብር 300.00 (ሶስት መቶ ብር) የአገልግሎት ክፍያ መክፈል አለባቸዉ፡፡ ከዚህ በተጨማሪ አዲስ የሙያ ፈቃድ ለማውጣት ሁለት ጉርድ ፎቶግራፍ፣ የጠፋባቸውን ለመተካትና ደረጃቸውን ለማሳደግ አንድ ጉርድ ፎቶግራፍ /3x4 መጠን/ ማቅረብ ይጠበቅባቸዋል፡፡
3) አዲስ የአማካሪ ድርጅት ፈቃድ ለማውጣት፣ የአማካሪ ድርጅት ደረጃ ለማሳደግና የጠፋን የድርጅት ፈቃድ በድጋሜ ለማውጣት ብር 500.00 (አምስት መቶ ብር) የአገልግሎት ክፍያ መከፈል አለበት፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ሁለት ጉርድ ፎቶግራፍ /3x4 መጠን/ ማቅረብ ይጠበቅባቸዋል፡፡
4) የአማካሪ ድርጅት ፈቃድ በየሁለት ዓመቱ ብር 300.00 (ሶስት መቶ ብር) የአገልግሎት ክፍያ በመክፈል፤ የሙያ ብቃት ማረጋገጫ ደግሞ ብር 200.00 (ሁለት መቶ ብር)በመክፈል ይታደሳል፡፡
5) የአማካሪ ድርጅት ፈቃድ ወይም የሙያ ብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት በተቀመጠው የጊዜ ገደብ ውስጥ ካልታደሰ በቀጣይ ሶስት ወራት ውስጥ ከአገልግሎት ክፍያ በተጨማሪ የቅጣት ብር 500.00 (አምስት መቶ ብር) እንዲከፍል በማድረግ እንዲታደስ ይደረጋል፡፡ በዚህ የጊዜ ገደብ ውሰጥ ሳይታደስ ከቀረ ለሚቀጥሉት ተጨማሪ ሶስት ወራት 800.00 (ስምንት መቶ ብር) ቅጣት እንዲከፍል በማድረግ እንዲታደስ ይደረጋል፡፡ በዚህ የጊዜ ገደብ ውስጥ ካልታደሰ የሙያ ብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀቱ ወይም የአማካሪ ድርጅቱ ፈቃድ ለአንድ አመት ይታገዳል፡፡
6) ነባር የሙያ ብቃት ማረጋገጫ ያላቸው ባለሙያዎች ይህ መመሪያ በወጣ በ6 ወራት ጊዜ ውስጥ አዲስ የማመልከቻ ፎርም በመሙላትና ያላቸውን ማስረጃ በማቅረብ አዲስ የሙያ ብቃትና የአማካሪ ደርጅት ፈቃድ ማውጣት አለባቸው፡፡ ይህ መመሪያ በወጣ በ6 ወራት ጊዜ ውስጥ ፈቃዳቸውን ለሚያሳድሱ አማካሪ ባለሙያዎች ምንም አይነት የአገልግሎት ክፍያ አይጠየቅም፡፡
7) ከ6 ወራት በኋላ ነባሩ የብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት ካልታደሰ የማያገለግል ሲሆን ከዚህ በኋላ ለሚቀርብ የፈቃድ ይታደስልኝ ጥያቄ ብር 300.00 (ሶስት መቶ ብር) የአገልግሎት ክፍያ እንዲከፍል እየተደረገ ይታደሳል፡፡ ይህም ሆኖ በአንድ አመት ጊዜ ውስጥ የብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀቱ ካልታደሰ የብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀቱ እንደተሰረዘ ይቆጠራል፡፡
2.4 የአካባቢ አማካሪ ድርጅቶችና ባለሙያዎች ተግባርና ኃላፊነት
1) የአማካሪ ድርጅት ፈቃድ ወይም የሙያ ብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት ከተሰጠበት ቀን ጀምሮ ሁለት ዓመት ከመሙላቱ ከሁለት ወራት በፊት ጀምሮ ሁለት ዓመት እሰኪሞላው ድረስ ለባለስልጣኑ ቀርቦ መታደስ አለበት፡፡ ሆኖም አንድ ባለሙያ መስሪያ ቤት ሲቀይር አዲሱ ስራው ከአማካሪነት ስራው ጋር የጥቅም ግጭት የሌለው መሆኑን ማረጋገጥ አለበት፡፡
2) አንድ የሙያ ብቃት ማረጋገጫ ማስረጃ የተሰጠው ባለሙያ በሁለት ድርጅቶች ውስጥ ተቀጥሮ መስራት ይችላል፡፡
3) አንድ የአካባቢ አማካሪ ድርጅት የቀጠራቸውን ባለሙያዎች ሙሉ ማስረጃ በየደረጃው ላለ የአካባቢ ጥበቃ መስሪያ ቤት የማስወቅ ግዴታ አለበት፡፡ የባለሙያ ለውጥ ሲኖር አማካሪ ድርጅቱ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ለሚመለከተው የአካባቢ ጥበቃ መስሪያ ቤት ለውጡን ማሳወቅ አለበት፡፡
4) አማካሪ ድርጅቱ ለአካባቢ ጥበቃ መስሪያ ቤት የሚያቀርበው ማስረጃ የባለሙያዎችን ሙሉ መረጃ፣ በድርጅቱ ውስጥ ያላቸውን ኃላፊነት፣ ስምና ፊርማ ያካተተ መሆን አለበት
5) አንድ አማካሪ ድርጅት የሚያዘጋጃቸውን ከአስር አመት ያነሰ የቆይታ ጊዜ ያላቸውን የተጽዕኖ ጥናት ዘገባዎች በሙሉ በመረጃ ቋት የማስቀመጥና በበጀት ዓመቱ ውስጥ ያዘጋጃቸውን የጥናት ሪፖርቶች አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን በሚያዘጋጀው የሪፖርት ቅጽ መሰረት ለባለስልጣኑ ሪፖርት የማድረግ ግዴታ አለበት፡፡
6) የአማካሪ ድርጅት ፈቃድ ወይም የሙያ ብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት የያዘ ማንኛዉም ሰዉ የምስክር ወረቀቱን ያለአግባብ ከተጠቀመበት ወይም የሌላን ሰው የብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት ያለአግባብ ተጠቅሞ ከተገኘ ወይም የሚጠቀምበትን የአማካሪነት ፈቃድ ማህተም ለሌላ አስተላልፎ/የራሱን ሰጥቶ/፣ ሀሰተኛ መረጃ አያይዞ ከተገኘ ባለስልጣኑ ወይም የሚመለከተዉ የአካባቢ ጥበቃ መስሪያ ቤት ፈቃዱ እንዲሰረዝና በህግ እንዲጠየቅ ያደርጋል፡፡
7) ከላይ የተገለጹት ተግባርና ኃላፊነቶች እንደተጠበቁ ሆኖ የሚከተሉት ጉዳዮች ሲያጋጥሙ የምስክር ወረቀቱ ይሰረዛል፡-
1) ምስክር ወረቀት የተሰጠው ባለሙያ ከዚህ ዓለም በሞት ሲለይ፣ ወይም በራሱ ጥያቄ ወይም በሌላ ምክንያት ስራውን ሲተው፣
2) አመልካቹ የምስክር ወረቀቱን ያገኘው በማጭበርበር መሆኑ ከተረጋገጠ፣
3) የምስክር ወረቀት የተሰጠው ድርጅት መክሰሩ ወይም መፍረሱ አግባብነት ባለው ፍ/ቤት ሲረጋገጥ ወይም በራሱ ምክንያት ስራውን አቁሞ የምስክር ወረቀቱን ሲመልስ፣
4) አመልካቹ ከብቃት ማረጋገጫ ምስክር ወረቀቱ ዓላማዎች ጋር የሚቃረኑ ተግባራትን ሲያከናውን ከተገኘ፣
5) የአማካሪ ድርጅቱ ለሰራው የአካባቢ ተፅዕኖ ዘገባ መልሶ የአካባቢ ኦዲት ሰርቶ ከተገኘ፣
6) ፈቃድ ባላገኘበት የማማከር ደረጃና ዘርፍ ተሰማርቶ ከተገኘ፣
😎 የሙያ ብቃት ማረጋገጫ ወይም የአማካሪ ድርጅት ፍቃድ የተሰጠው አካል በሰው ወይም በድርጅት ላይ ሆነ ብሎ ወይም በቸለልተኝነት ሙያው የሚጠይቀውን ሥነ-ምግባር በመጣስ ስራውን ተገቢ ባልሆነ አሰራር ያከናወነ ስለመሆኑ ከተጠቃሚዎች በህግ የተረጋገጠ ማስረጃ ሲቀርብ፤ የሌላ ሰውን ስራ የራሱ አስመስሎ የቀዳ ወይም የገለበጠ፤ እንደ ጥፋቱ ደረጃ ከአንድ አመት እገዳ እስከ ምስክር ወረቀት ስረዛ የሚደርስ እርምጃ ይወሰዳል፡፡
9) አንድ የአካባቢ አማካሪ ድርጅት በባለስልጣን መስሪያ ቤቱ የሙያ ብቃት ማረጋገጫ ሰርተፊኬት አግኝቶ የአማካሪነት ስራ ሲሰራ የሚያቀርባቸው የአካባቢ ተጽዕኖ ጥናት ዘገባዎች ላይ በተደጋጋሚ የጥራት ችግር የሚያጋጥም ከሆነ በመጀመሪያ የቃል ማስጠንቀቂያ፣ ቀጥሎም የጽሁፍ ማስጠንቀቂያ ከተሰጠው በኋላ የሰነዱን ጥራት የማያስተካክል ሆኖ ሲገኝ ባለስልጣኑ የሰጠውን የአካባቢ የሙያ ብቃት ማረጋገጫ ሰርተፊኬት በመሰረዝ የአካባቢ አማካሪነት ስራውን እንዲያቋርጥ ያደርጋል፡፡
10) አንድ ሰው የተለያዩ የአካባቢ አማካሪነት የሙያ ፈቃዶች ካሉት በአንድ ጥናት ውስጥ መሳተፍ የሚችለው በአንዱ የሙያ ፈቃድ ብቻ ይሆናል፡፡ የትምህርት ዝግጅቱ ፈቅዶለት ከአንድ በላይ የብቃት ማረጋገጫ ምስክር ወረቀት ያገኘ ባለሙያ አንድ ሰነድ ዝግጅት ላይ ከአንድ መስክ በላይ ከተሠማራ ለአንድ አመት እገዳ ይጣልበታል፡፡
11) አንድ አማካሪ ድርጅት የራሱን የልማት ፕሮጀክት በአማካሪነት ሊሰራ አይፈቀድለትም፡፡ በመሆኑም ገለልተኛ በሆነ የአካባቢ አማካሪ ድርጅት አሰርቶ ማቅረብ አለበት፡፡ አንድ አማካሪ ድርጅት የራሱን የልማት ፕሮጀክት ሲሰራ ከተገኘ ለአንድ አመት እገዳ ይጣልበታል፡፡
2.5 ለምዝገባ መሟላት ያለባቸው ጉዳዮች
1) ማንኛዉም የሙያ ብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት ለማዉጣት የሚቀርብ አመልካች በቅድሚያ ባለስልጣኑ ያዘጋጀዉን የምዝገባ ፎርም ሞልቶ ማቅረብ አለበት፡፡
2) የሙያ ብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት ለሚያወጡ ባለሙያዎች ሁለት የቅርብ ጊዜ 3x4 መጠን ያለዉ ጉርድ ፎቶ ግራፍ ማቅረብ አለባቸው፡፡
3) አዲስ የአካባቢ አማካሪነት ድርጅት ፈቃድ የምስክር ወረቀት እንዲሰጠው ጥያቄ ያቀረበ ድርጅት በባለስልጣኑ መስሪያቤት የተሰጠና የታደሰ የሙያ ብቃት ማረጋገጫ ምስክር ወረቀት እንዲሁም የታደሰ የቀበሌ መታወቂያ ከአንድ ፎቶ ኮፒ ጋር ማቅረብ ይኖርበታል፡፡
4) የምስክር ወረቀት እንዲሰጣቸው ጥያቄ ያቀረቡ የድርጅት ባለቤቶች ከአንድ ግለሰብ በላይ ከሆኑ ስልጣን ባለው አካል የፀደቀ የድርጅት መመስረቻ ሰነድ፣ መተዳደሪያ ደንብ እና ማመልከቻውን ይዞ የቀረበው ሰው የውክልና ማስረጃ ከአንድ ፎቶ ኮፒ ጋር ማቅረብ አለበት፡፡
5) የአንድ አማካሪ ድርጅት የአማካሪነት ደረጃ በዚህ መመሪያ በዕዝል 15.7 በተዘረዘሩት የመመዘኛ መስፈርቶች መሠረት ተፈፃሚ ይሆናል፡፡
6) ደረጃው እንዲሻሻል የጠየቀ አማካሪ ድርጅት በዚህ መመሪያ መሠረት ማሟላት ያለበት የባለሙያ ዓይነትና ብዛት በዕዝል 15.7 የተገለጸ ሲሆን፤ የታደሰ የባለሙያዎች የቀበሌ መታወቂያ ከአንድ ፎቶ ኮፒ ጋር፣ የታደሰ የብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት ከአንድ ፎቶ ኮፒ ጋር እንዲሁም ከተቀጣሪ ባለሙያዎች ጋር የተደረገ የስራ ውል ስምምነት ከአንድ ፎቶ ኮፒ ጋር ማቅረብ አለበት፡፡
7) አዲስ የአካባቢ አማካሪ ድርጅት ፈቃድ የምስክር ወረቀት እንዲሰጠው ጥያቄ ያቀረበ ድርጅት የመስሪያ ቢሮ ያለው መሆኑን ማረጋገጫ ሰነድ ወይም ሕጋዊ የቤት ኪራይ ውል ከአንድ ፎቶ ኮፒ ጋር እና የድርጅቱ ባለቤት ወይም የድርጅቱ ስራ አስኪያጅ 3x4 የሆነ ሁለት ፎቶ ግራፍ ማቅረብ አለበት፡፡
😎 አዲስ የሙያ ብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት ለማውጣት የሚቀርብ ማመልከቻ የአመልካቹን ዋና የትምህርት ማስረጃና የሥራ ልምድ ከአንድ ፎቶ ኮፒ ጋር አያይዞ ማቅረብ አለበት፡፡
9) በመንግስት ወይም በግል መስሪያ ቤት ወይም ድርጅት በቋሚነት ተቀጥረው የሚሰሩ ባለሙያዎች በተቋማቸው የሚሰሩት ስራ የሙያ ፈቃድ ከሚጠይቁበት የአማካሪነት ስራ ዘርፍ ጋር የጥቅም ግጭት የማይፈጥር መሆኑን ወይም የማማከር ስራ እንዲሰሩ ስለመፍቀዱ ከሚሰሩበት መስሪያ ቤት/ድርጅት የጽሁፍ ማረጋገጫ ወይም የድጋፍ ደብዳቤ ማቅረብ አለባቸዉ፡፡
2.6 የአማካሪ ድርጅት ወይም የሙያ ብቃት ማረጋገጫ ሰርተፊኬት አሰጣጥ ሂደት
1) የአማካሪ ድርጅት ወይም የሙያ ብቃት ማረጋገጫ ሰርተፊኬት ይሰጠኝ ማመልከቻ ለባለስልጣኑ ቀርቦ ለባለሙያዎች በተመራ በ4 ቀናት ውስጥ የማስረጃ ሰነዱ ተግምግሞ ለውሳኔ ይቀርባል፡፡ የሚቀርበው ማመልከቻ በእዝል 15.8 ላይ በተያያዘው ቅጽ መሰረት የሚቀርብ ይሆናል፡፡
2) የቀረበው የማመለክቻ ሰነድ ከተመረመረ በኋላ ውጤቱ ላይ ኃላፊው ወይም ዳይሬክተሩ የፈረበት ውሳኔ ማስታወቂያ ሰሌዳ ላይ ለ5 ቀናት ተለጥፎ እንዲቆይ ይደረጋል፡፡
3) አንድ ባለሙያ ከሁለት የሙያ ዘርፎች በላይ ፈቃድ ሊወስድ አይችልም እንዲሁም ከሁለት አማካሪ ድርጅቶች በላይም በመስራች አባልነት ሊመዘገብ አይችልም፡፡
4) የአማካሪ ድርጅቱ ወይም አመልካቹ ባለሙያ ያላሟላቸው ሰነዶች ካሉ እንዲሟሉ በስልክ/ በማስታወቂያ ይነገረዋል፤ የማለፊያ ውጤቱን ላገኘ አመልካች ደግሞ ውሳኔ በተሰጠ በ10 ቀናት ውስጥ የሙያ ፈቃድ/ የብቃት ማረጋገጫ ሰርተፊኬቱ ይሰጠዋል፡፡
5) አንድ የሙያ ብቃት ማረጋገጫ ሰርተፊኬት ይሰጠኝ ብሎ የሚጠይቅ ጀማሪ ባለሙያ የአማካሪነት የምስክር ወረቀት የሚሰጠው ዝቅተኛ የማለፊያ ነጥብ የሆነውን 50% ውጤት ሲያገኝ ሲሆን የከፍተኛ አማካሪነት የምስክር ወረቀት የሚሰጠው በመመዘኛዎች መሰረት ዝቅተኛ የማለፊያ ነጥብ የሆነውን 70% ውጤት ሲያገኙ ነው (መስፈርቱን በዕዝል 15.5 ይመልከቱ)
6) አንድ የሙያ ብቃት ማረጋገጫ ሰርተፊኬት ይሰጠኝ ብሎ የሚጠይቅ ባለሙያ በአቀረበው ማስረጃ ማለፍ ካልቻለ በድጋሜ ማመልከት የሚችልው ከአንድ ዓመት የቆይታ ጊዜ በኋላ ይሆናል፡፡ የተጭበረበረ ማስረጃ አያይዞ የሚያቀርብ ባለሙያ ካለ የብቃት ማረጋገጫ ሰርተፊኬት እንዳይሰጠው እገዳ ይደረግበታል፡፡
7) በደረጃ I እና በደረጃ II የአካባቢ አማካሪ ድርጅት ፈቃድ ለማውጣት የሚያመለክቱ አካላት የአማካሪነት ፈቃድ ለማግኘት በዚህ መመሪያ ዕዝል 15.7 ላይ የተገለጸውን ዝቅተኛ መስፈርት ማሟላት ይጠበቅባቸዋል፡፡
😎 አንድ የሙያ ብቃት ማረጋገጫ ሰርተፊኬት የተሰጠው ባለሙያ ወይም ፍቃድ የተሰጠው አማካሪ ድርጅት የደረጃ ይሻሻልልኝ ጥያቄ ማቅረብ የሚችለው ከአንድ ዓመት የቆይታ ጊዜ በኋላ ይሆናል፡፡
2.7 ስለምስክር ወረቀት አሰጣጥና ይዘት
1) በዚህ መመሪያ ውስጥ የተዘረዘሩ መስፈርቶች ላሟላ ባለሙያ ወይም አማካሪ ድርጅት የአማካሪነት የምስክር ወረቀቱ ይሰጠዋል፡፡
2) በባለስልጣን መስሪያ ቤቱ የሚሰጥ የብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት እንደ አግባቡ የሚከተሉትን መረጃዎች መያዝ አለበት፡፡
1) የባለሙያውን /የድርጅቱን ሙሉ ስም፣
2) የስራ አድራሻ፣
3) የብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት የተሰጠበት የማማከር አገልግሎት ዘርፍ
4) የምስክር ወረቀቱ ደረጃ፣
5) የምስክር ወረቀቱ የተሰጠበት ቀን፣
6) የምስክር ወረቀቱ ፀንቶ የሚቆይበት የጊዜ ገደብ፣
7) የባለሙያውን ፎቶ ግራፍ (የድርጅቱን ባለቤት) የስራ አስኪያጅ ፎቶ ግራፍ፣
😎 መለያ ቁጥር፣
9) የፈቃድ ሰጪውን ኃላፊ ስም፣ ፊርማና የባለስልጣኑ መሰሪያ ቤት ማኅተም፣
2.8 ስለቅሬታ አቀራረብ
1) በውሳኔ አሰጣጡ ቅር የተሰኘ ማንኛውም አመልካች ውሳኔው በተገለፀ በ5 ቀናት ውስጥ ቅሬታውን በጽሁፍ ለባለስልጣኑ ማቅረብ ይችላል፡፡ አመልካቹ በ5 ቀናት ውስጥ ቅሬታውን ካላቀረበ ውሳኔውን እንደተቀበለ ይቆጠራል፡፡
2) ቅሬታ የቀረበለት ባለሙያ ወይም ኃላፊ በ10 ቀናት ውስጥ ቅሬታውን መርምሮ ምላሽ መስጠት አለበት፡፡
3) ባለሙያው ወይም ኃላፊው ቅሬታውን መርምሮ በሰጠው ውሳኔ ላይ ቅር የተሰኘ አመልካች ቅሬታውን ለሚመለከተው አካል ማቅረብ ይችላል፡፡
3 የይሁንታ ፈቃድ ሳይዙ ወደ ተግባር የገቡና የሚገቡ ፕሮጀክቶችን አሰራር ስለመወሰን
የአካባቢ ይሁንታ ሳይሰጣቸው ወደ ትግበራ የገቡ (የሚገቡ) ፕሮጀክቶች አካባቢን እየበከሉና ማህበረሰብን እየጎዱ መቀጠል ስሌለባቸው አዋጅ ቁጥር 181/2003 ዓ.ም አንቀጽ 6 (1ሐ) ህጉን ተፈፃሚ በማድረግ የሚደርሰውን ጉዳት መከላከል (ማስቀረት) የሚያስችል ስርዓት በመዘርጋት ተግባራዊ ይደረጋል፡፡ በመሆኑም፡-
1) አዋጅ ቁጥር 181/2003 ዓ.ም አንቀጽ 6 (1ሐ) መሰረት የተሰጠውን የዕፎይታ ጊዜ በመጠቀም የአካባቢ አያያዝ ዕቅድ ሳያዘጋጅና ይሁንታ ሳያገኝ ወደተግባር ገብቶ የተገኘ ፕሮጀክት ከሃምሳ ሺህ ብር እስከ አንድ መቶ ሺህ ብር የገንዘብ ቅጣት ይቀጣል፡፡ ቅጣቱን ከፈጸመ በኋላም በ3 ወራት ጊዜ ውስጥ የፕሮጀክቱን የአካባቢ ምርመራ በራሱ ወጭ በማካሄድ ችግሩን (ተጽዕኖውን) የሚያቃልል የአካባቢ አያያዝ ዕቅድ አዘጋጅቶ በማቅረብ ይሁንታ ሰርተፊኬት ማግኘት አለበት፡፡
2) በዚህ መመሪያ በተራ ቁጥር 10.1 የተገለፀው እንደተጠበቀ ሆኖ የፕሮጀክት ባለቤቱ በተሰጠው የጊዜ ገደብ ውስጥ የአካባቢ አያያዝ ዕቅድ በማቅረብ ይሁንታ ሰርተፊኬት ሳያገኝ የቀረ እንደሆነ ከመቶ ሃምሳ ሺህ ብር በማያንስና ከሁለት መቶ ሺህ ብር በማይበልጥ የገንዘብ መቀጮ ይቀጣል፡፡
3) ፕሮጀክቱ በአካባቢና በማህረሰቡ ላይ ጉዳት ወይም ብከለት ያደረሰ እንደሆነ በሌሎች ህጎች የሚጠየቅ መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ የንግድ ፈቃዱ ለተወሰነ ጊዜ እንዲታገድ ወይንም ሙሉ በሙሉ እንዲሰረዝ ለፈቃድ ሰጪ መስሪያ ቤቱ በደብዳቤ ይገለፃል፡፡ ደብዳቤው የደረሰውም የንግድ ፈቃድ ሰጪ መስሪያቤት የሰጠውን የንግድ ፈቃድ ማገድ ወይንም መሰረዝ ይኖርበታል፡፡ የአካባቢ ግብረ-ሀይልም ይህ የማገድ (የመዘረዝ) ውሳኔ ተግባራዊ እንድሆን የማድረግ ኃላፊነት አለበት
4) የአካባቢ ተፅዕኖ ግምገማ አዋጅ ቁጥር 181/2003 አንቀጽ 25/2 መሰረት አዋጁ ከወጣ በኋላ የአካባቢ ተፅዕኖ ግምገማ የጥናት ዘገባ ሳያቀርብና የይሁንታ ፈቃድ ሳያገኝ ወደ ተግባር የገቡ ፕሮጀክት ከሃምሳ ሺህ ብር በማያንስና ከመቶ ሺህ ብር በማይበልጥ የገንዘብ መቀጮ ተቀጥቶ በ3 ወራት ጊዜ ውስጥ የፕሮጀክቱን የአካባቢ ምርመራ በማካሄድ ተጽዕኖውን የሚያቃልል የአካባቢ አያያዝ ዕቅድ አዘጋጅቶ በማቅረብ የይሁንታ ሰርተፊኬት ማግኘት አለበት፡፡ ይህ ካልሆነ የፕሮጀክቱ ስራ ለጊዜው እንዲቋረጥ ተደርጎ የአካባቢ አያያዝ እቅድ በተሟላ መንገድ ተዘጋጅቶ በሚመለከተዉ አካል ተቀባይነት ሲያገኝ ፕሮጀክቱ እንደገና ስራ እንዲጀምር ይደረጋል፡፡ በአካባቢ ክትትልና ቁጥጥር በሰውና አካባቢ ላይ ጉዳት ማድረሱ ከተረጋገጠ በወንጀልና በፍታብሔር ህጎች እንዲጠየቅ ይደረጋል፡፡
5) በዚህ መመሪያ በተራ ቁጥር 10.3 የተገለፀው እንደተጠበቀ ሆኖ የፕሮጀክት ባለቤቱ የአካባቢ አያያዝ ዕቅድ በማቅረብ የይሁንታ ሰርተፊኬት ሳያገኝ የቀረ እንደሆነ አግባብ ባላቸው ህጎች መጠየቁ እንደተጠበቀ ሆኖ የንግድ ፈቃዱ እንዲሰረዝ ለፈቃድ ሰጪ መስሪያ ቤቱ በደብዳቤ ይገለፃል፡፡ ደብዳቤው የደረሰውም የንግድ ፈቃድ ሰጪ መስሪያ ቤት የሰጠውን የንግድ ፈቃድ መሰረዝ ይኖርበታል፡፡ የአካባቢ ጥበቃ ግብረ ሀይልም የማገድ/ የመዘረዝ ውሳኔ ተግባራዊ እንዲሆን የማድረግ ኃላፊነት አለበት፡፡
6) ፕሮጀክቱ በአካባቢና በማህረሰቡ ላይ ጉዳት ወይም ብከለት ያደረሰ እንደሆነ አግባብ ባላቸው ህጎች መጠየቁ እንደተጠበቀ ሆኖ የስራ/የንግድ ፈቃዱ እንዲሰረዝ ለፈቃድ ሰጪ መስሪያ ቤቱ በደብዳቤ ይገለፃል፡፡ ደብዳቤው የደረሰውም የስራ/የንግድ ፈቃድ ሰጪ መስሪያቤት የሰጠውን የስራ/የንግድ ፈቃድ መሰረዝ ይኖርበታል፡፡ የአካባቢ ጥበቃ ግብረ ሀይልም የማገድ/ የመዘረዝ ውሳኔ ተግባራዊ እንዲሆን የማድረግ ኃላፊነት አለበት፡፡
7) በዚህ መመሪያ የተደነገገዉ እንደተጠበቀ ሆኖ በሕግ የሰውነት መብት የተሰጠው ድርጅት ጥፋት ሲፈፅም ድርጅቱ እንዲከፍለው ከተፈረደበት መቀጮ በተጨማሪ የአካባቢ ህጉን ማስከበር የነበረበት ኃላፊ/መሪ መፈፀም የሚገባውን ተግባር በትጋት ያልተወጣ በመሆኑ ከአምስት ሺህ ብር በማያንስና ከአስር ሺህ ብር በማይበልጥ የገንዘብ መቀጮ ወይንም ከአንድ አመት በማያንስ ከ3 ዓመት በማይበልጥ እስራት ወይም በሁለቱም ይቀጣል፡፡
😎 አዋጅ ቁጥር 181/2003 ዓ.ም ወይም በሥሩ የወጣዉን ይህን መመሪያ በመጣስ ጥፋተኛነቱ የተረጋገጠበትን ሰው/ድርጅት ከሚወሰንበት ከማንኛውም ቅጣት በተጨማሪ የደረሰውን ጉዳት በሙሉ በራሱ ወጪ እንዲያስተካክል ወይም እንዲተካ እና ካሳ እንዲከፍል ስልጣን ያለው ፍርድ ቤት ማዘዝ ይችላል፡፡
9) በዚህ መመሪያ በተራ ቁጥር 10.6፣ 10.7 እና 10.8 የተደነገገዉ እንደተጠበቀ ሆኖ ፕሮጀክቱ በአካባቢ ላይ ያደረሰዉ ጉዳት ከፍተኛ ከሆነ ፕሮጀክቱ እንዲቋረጥ፣ እንዲዘረዝ ወይም የቦታ ለዉጥ እንዲያደርግ ባለስልጣኑ ወይንም በዞንና በወረዳ ያሉ የአካባቢ ጥበቃ መ/ቤቶች ሊወስኑ ይችላሉ፡፡ የአካባቢ ጥበቃ ግብረ ሀይልም ይህ ውሳኔ ተግባራዊ እንዲሆን የማድረግ ኃላፊነት አለበት፡፡
10) በዚህ መመሪያ በተራ ቁጥር 10.6፣ 10.7 እና 10.8 የተደነገገዉ እንደተጠበቀ ሆኖ ፕሮጀክቱ ያደረሰው ጉዳት ከፍተኛ ካልሆነ እና በተፅዕኖ ማቅለያ መቀነስ የሚቻል ከሆነ በ3 ወራት ጊዜ ውስጥ የአካባቢ አያያዝ ዕቅድ በማዘጋጀት ይሁንታ ሰርተፊኬት እንዲያገኝ ይደረጋል፡፡ የአካባቢ አያያዝ ዕቅድ አቅርቦ ይሁንታ ሰርተፊኬት የማያገኝ ከሆነ ግን ፕሮጅከቱ እንዲሰረዝ ይደረጋል፡፡
11) በተራ ቁጥር 10.1፣ 10.3፣ 10.4 እና 10.10 የተጠቀሱት እንደተጠበቁ ሆኖ ፕሮጀክቶች የአካባቢ አያያዝ ዕቅድ ካዘጋጁ በኋላ የተዘጋጀዉን የአካባቢ አያያዝ ዕቅድ ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስቸግር አዲስ ሁኔታ ወይም አሰራር የሚከሰት ከሆነ የአካባቢ አያያዝ ዕቅዱ መከለስና በሚመለከተዉ አካል በኩል እንደገና መጽደቅ አለበት፡፡
12) አንድ የአካባቢ አያያዝ እቅድ የሚያገለግልበት የጊዜ ርዝማኔ ጣሪያ 10 ዓመት ሲሆን የ3 ዓመት የዝርዝር ተግባራት የድርጊት መርሀ ግብር ይኖረዋል፡፡ የዝርዝር ተግባራት እቅድ በየ 3 ዓመቱ የሚዘጋጅ ሲሆን ከአስር አመት በኋላ ሰነዱ ሙሉ በሙሉ በአዲስ መልክ የሚከለስ ይሆናል፡፡
ይቀጥላል…………………….

Address

Dessie
033

Opening Hours

Monday 02:30 - 11:00
Tuesday 02:30 - 11:00
Wednesday 02:30 - 11:00
Thursday 02:30 - 11:00
Friday 02:30 - 11:00
Saturday 02:30 - 11:00

Telephone

+251912072360

Website

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when ወሎ የአካባቢ ተጽዕኖ ግምገማ -Wollo EIA posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Business

Send a message to ወሎ የአካባቢ ተጽዕኖ ግምገማ -Wollo EIA:

Share