20/08/2026
🙏🙏🙏
የደብረ ታቦር በዓል በቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዘጠኙ ዐበይት በዓላት አንዱ ነው፡፡ ከዐበይት በዓላት የተመደበበትም ምክንያት በደብረ ታቦር የተገለጸው ምሥጢር ድንቅ በመሆኑ ነው። ደብረ ታቦር ከገሊላ ባሕር በምዕራባዊ በኩል 10 ኪሎ ሜትር ርቆ የሚገኝ ተራራ ሲሆን፤ ከፍታው ከባሕር ወለል በላይ 572 ሜትር ይሆናል፡፡ በዚህ ተራራ ላይ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብርሃነ መለኮቱን እንደሚገልጽ ምሳሌና ትንቢት ተነግሯል፡፡
ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት በትንቢቱ "ታቦርና አርሞንዔም በስምህ ደስ ይላቸዋል" ብሎ የተናገረው ትንቢት እንዲፈጸም ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተአምራቱን በዚህ ተራራ ላይ ገልጧል። መዝ. 88፥12 በዘመነ መሳፍንት ባርቅ ሲሣራን ከነሠራዊቱ ድል ያደረገው በደብረ ታቦር ተራራ ላይ ነው፡፡ ምሳሌነቱም ባርቅ የጌታችን ሲሣራ ደግሞ የአጋንንት ነው፡፡
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዛሙርቱን በቂሳርያ "ሰዎች የሰውን ልጅ ማን ይሉታል?" ብሎ ከጠየቃቸው ከስድስት ቀን በኋላ አዕማድ ተብለው የሚጠሩ ሦስቱን ሐዋርያት ይዞ ወደ ረጅም ታቦር ተራራ ወጣ፡፡ በፊታቸውም ተለወጠ ፊቱም እንደ ፀሐይ በራ ልብሱም እንደ ብርሃን ነጭ ሆነ፡፡ እነሆም ሙሴና ኤልያስ ከእርሱ ጋር ሲነጋገሩ ታዩአቸው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ መልሶ ጌታችንን "ጌታ ሆይ በዚህ መሆን ለእኛ መልካም ነው፡፡ ብትወድስ በዚህ ሦስት ዳስ እንሥራ አንዱን ለአንተ አንዱን ለሙሴ አንዱን ለኤልያስ" አለ፡፡ በዚህ ጊዜ ብሩህ ደመና ጋረዳቸው፡፡ ከደመናውም "በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው፡፡ እርሱን ስሙት" የሚል ድምፅ ተሰማ፡፡ ሐዋርያት ይህንን ሰምተው የጌታችንን መለኮታዊ ክብር ዓይተው በፊታቸው ወደቁ እጅግ ፈርተው ነበር፡፡ ጌታችንም ተነሡ አትፍሩም አላቸው፡፡ በዚህ መልኩም አምላክነቱን ገለጠላቸው። ማቴ. 17፥1-10
ሦስቱ ሐዋርያት ለምን ተመረጡ?
አዕማደ ሐዋርያት ተብለው የተጠሩት ጴጥሮስ፣ ያዕቆብና ዮሐንስ ናቸው፡፡ ገላ. 2፥9 ስያሜውን ያገኙበት ዋናው ምክንያት ጌታችን በኢያኢሮስ ቤት ልጁን ሲፈውስ፣ በጌቴ ሴማኒ ሲጸልይና በደብረ ታቦር ምሥጢረ መለኮቱን ሲገልጥ ከእሱ ስላልተለዩና ይዟቸው ስለሔደ ነው። ማር.5፥37-43
ሙሴና ኤልያስ ለምን ተመረጡ?
ሙሴንና ኤልያስን ወደ ደብረ ታቦር እንዲመጡ ያደረገበት ምክንያት የባሕርይ አምላክ መሆኑን እንዲመሰክሩ ነው፡፡ ሙሴን ከመቃብር ተነሥቶ ኤልያስ ደግሞ ከብሔረ ሕያዋን መጥቶ የባሕርይ አምላክነቱን መስክረዋል፡፡
ሙሴና ኤልያስ የተመረጡበት ሌላው ምክንያት ሙሴ "ጀርባዬንም ታያለህ ፊቴ ግን አይታይም" ተብሎ ስለተነገረለት (ዘፀ.33፥23) ኤልያስ "በኋለኛው ዘመን ምስክሬ ትሆናለህ"ስለተባለ ያንን ለመፈጸም ነው፤ ካገቡት ሙሴን ከደናግል ኤልያስ ያመጣቸው መንግሥተ ሰማያት በሕግ የተጋቡ ሕጋውያንና ሥርዐት ጠብቀው የሚኖሩ ደናግላን እንደሚወርሷት ለማስተማር ሁለቱን መርጧቸዋል፡፡
የደብረ ታቦር ምሳሌ
ደብረ ታቦር የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ነች። ተራራ መሠረቱ ከመሬት አናቱ ከሰማይ እንደሆነ ሁሉ ቤተ ክርስቲያንም መሠረቷ በምድር ሲሆን ራሷ በሰማይ ነውና። በሰማይ ካሉት ሙሴና ኤልያስን ከምድር ካሉት ጴጥሮስን ያዕቆብን፣ ዮሐንስን ሰብስባለችና፡፡ አንድም የወንጌል ምሳሌ ነው፡፡ ተራራ ሲወጡት አድካሚ ነው ከወጡት በኋላ ግን ሁሉንም ቁልጭ አድርጎ ሲያሳይ ደስ ያሰኛል፤ ወንጌልም ሲማሯት፤ ሲያስተምሯት ታደክማለች፤ ከተማሯት በኋላ ግን ጽድቅና ኀጢአትን፤ እውነትንና ሐሰትን ለይታ ስታሳውቅ ደስ ታሰኛለችና።